Tuesday 24 September 2019

የመደመር ቀለም አብዮትና መዘዙ: በትግራይ ህዝብ ላይ ያነጣጠረ እንደገና አዲስ የቀለም አብዮት እየተሸረበ ነው!

ዑስማን ሙለዓለም:
 ከሐራ ገበያ
መስከረም 2012 /

መግብያ
የአብይ መንግስት በመደመር የቀለም አብዮት ስትራተጂና የታክቲክ ጥበብ እንቅስቃሴ እውን ከሆነ ድፍን ዓመቱ አሳልፎ ሁለተኛ አዲስ ዓመት በቤተመንግስት አክብሯል። በመጀመርያ አከባቢ የቀለም አብዮቱ መሪዎች፣ ቁልፍ ተባባሪዎቻቸው እና ተከታዮቻቸው በውጤቱ ጮቤ ረግጠው ደስታቸውን በሁሉም መንገድ ገልፀው ነበር። ይሁን እንጂ እንደ ሁሉም በዓለማችን የተፈፀሙ የቀለም አብዮቶች የድል ተገኘ ፈንጠዝያው ረገብ እያለ ሲሄድ ሁኔታዎች ከመቅፅበት ወደ ሐዘን ወይም ወደ ያልታሰበ ፈጣን የውድቀት ጉዞ እንደተቀየሩት የአገራችንም ፈንጠዝያ ወደ ዋይታ የተቀየረው ወዲያውኑ ነበር።

የዩክሬን ብርቱካናማው ቀለም አብዮትና የአረብ የፀደይ አብዮት በቱኑዝያ፣ በሊብያ፣ በግብፅ፣ በየመንና በሶርያ ያስከተሉት ሁኔታ ይህንኑ ነው፡፡ በየአገራቱ በቀለም አብዮቱ የተነሱት የዲሞክራሲና የዳቦ ጥያቄዎች እንኳን ሊመለሱ የነበራቸው ሰላም ማስፈን አልቻሉም፡፡ የቡዙ ሰዎች መፈናቀል፣ ስደትና ሞት የበዛበት፣ የሃብትና የንብረት ውድመት ያስከተለበትና ሀገሮች እንደ አገር መቆም አቅታቸው ብዙዎቹ የመፈራረስ አደጋ አጋጥማቸዋል፡፡ እንደ ግብፅ ያሉት ደግሞ እንደ አገር ቢቀጥሉም ወደ ዴሞክራሲ ሳይሆን ከሙባረክ ወደ የኮ/ል አሻግሬ ጌታ አል ሲሲ አምባገነናዊ መንግስት ይሸጋገራሉ። መሸጋገር ከሆነ።

ስለ ቀለም አብዮት በአጭሩ
የቀለም አብዮት በጥሩ ቀለሞችና ስሞች አሸብርቆ ከውጭ ታቅዶ፣ ተሰርቶ፣ ወደ ዒላማ የተደረገ አገር የሚመጣ አብዮት (imported revolution) ወይም ለውጥ ወይም ሪፍርም ነው፡፡ በመሆኑ በዘለቄታው ስኬታማ ሊሆን አይችልም። ከውጭ መምጣቱ ብቻ ግን ለውድቀቱ ምክንያት አይደለም። የሚጠቀምባቸው ስትራተጂዎችና ታክቲኮችም ስርዓት ለማፍረስ እንጂ ስርዓት ለመገንባት የሚዉሉ ስላልሆኑ በተካሄዱባቸው አገሮች አገር ለመገንባትና ዲሞክራሲ ለማስፋፋት ውጤታማ ሲሆኑ አይታዩም።

የቀለም አብዮት ባለቤቶች አክራሪ የኒዮ ሌበራሊዝም ሐይሎች ናቸው፡፡ እነዚህ ሐይሎች የራሳቸው ጥቅም መሰረት አድርገው ተፅእኖ ለመፍጠር እንጂ ከልብ የሌሎች አገሮች ህዝብ ችግር አስጨንቃቸው ወይም ርህራሄ ስላላቸው የሚያቅዱት አብዮት ወይም ለውጥ አይደለም። የቀለም አብዮት የድሮው ቅኝ ግዛት ፍልስፍና ተቀጥያ የሆነና ዘመናዊ ቅኝ ግዛት መፍጠርያና ማስፋፍያ ዘዴ ነው። የራስህ ተላላኪ አሻንጉሊት መንግስት በመፍጠር የተፅዕኖህ አድማስ በዓለም ደረጃ ማስፋፋት ዓላማ ያለው ነው። የቀለም አብዮት የልዕለ ሐያላን አክራሪ ኒዮ ሌበራሎች ገበያቸውን ለማስፋት በሚያደርጉት ውድድር አሸንፎ ለመውጣት የባህል፣ የአይዶሎጂና የፖሊሲ ወረራ ማስፈፀሚያ መሳርያ ነው። ከራሻና ከቻይና ጋር ሆኑ/ ወገኑ ወይም ፖሊሲያቸው ለኛ አይመችም ብለው ከሚፈርጅዋቸው አገሮች ላይ ፈርደው የቀለም አብዮት ያፋፍማሉ። ለውጥ ብለው አገር የሚያፈርስ ነውጥ ይፈጥራሉ።

የቀለም አብዮት ቀያሽና ጠንሳሽ ሐይሎች የሚጠቀምቧቸው ሰዎችና ቁልፍ ተባባሪዎቻቸው የራሳቸው ጥቅም ብቻ አፍቃሪ ናቸው፡፡ እንኳን የህዝብ ፍቅር ሊኖሯቸው ተራ የአገር ፍቅርም የሌላቸው ምላስ አደሮች ናቸው፡፡ የማይታመኑ፣ በውሸትና በቅጥፈት የሚታወቁና በዶላር የተሸመቱ ስለሆኑ ቁርጠኝነታቸው ከግል ስግብግብ ዓላማ መፈፀም ያለፉ ስላልሆኑ ለማህበረሰብ መሰረታዊ ለውጥና ለዴሞክራሲ ግንባታ ከጉንጭ ማልፋት ያለፈ አይጨነቁም። እነዚህ ከላይ ከላይ የለውጥ ቀለም ከመቀባትና ከማንፀባረቅ አልፈው የሰፊውን ህዝብ ኑሮ መብት ጥያቄ አይቀይሩም። አይመልሱም።

የነሱ አቅም የሚያስጎመጁና የሚያማልሉ የቀለሞ አይነቶች ወይም ወቅቶችን ስያሜዎችን ማውጣት ነው፡፡ ለምሳሌ ብርቱካናማው አብዮት፣ የፀደይ አብዮት፣ የቀስተደመና አብዮት እና የመደመር አብዮት ብለው የህዝቡን ቀልብ ሰርቀው ስልጣን መወጣጫ ይጠቀሙበታል፡፡ ይሁን እንጂ እንደስሙ ለውጡ/አብዮቱ የቀለም መልክ እንጂ የቁምነገርና የይዘት ለውጥ የለውም። የነበረው የህዝብ መብትና ሀብት ያጠፉታል እንጂ ምንም አዲስ ጠብ የሚል የኢኮኖሚን የዲሞክራሲ ለውጥ አያስመዝግቡም። በለውጡ ስም ሁሉንም ነገሮች ባልተጠናና በውጭ ሐይሎች ትዕዛዝ ስለሚነካካ ያልታሰቡ ችግሮች እየተፈጠሩ ለውጥ መሆኑ እየቀረ ነውጥና የማያቋርጥ ቀውስ ውስጥ ይከታል።

ሚልዮኖች ዶላር ከውጭ በማፍሰስ ማህበረሰባዊ ለውጥ ማምጣትና ዲሞክራሲ መትከል አይቻልም። ለውጥ ከውስጥ ካልሆነ ስኬታማ ሊሆን አይችልም። ቀላል ምሳሌ እንይ። ደሮ እንቁላሎች ታቅፋ ሙቀት ከራስዋ ወደ እንቁላለቹ በማስተላለፍ በቂ ሙቀት እንዲያገኙ ካደረገች በኃላ የተፈጥሮ ጊዜውን ጠብቆ ጫጩቶች ይፈለፈላሉ። ነገር ግን በእንቁላል ፋንታ የእንቁላል ቅርፅና መጠን ያላቸው ድንጋዮች በተመሳሳይ ሁኔታ ብናሳቅፋት የደሮዋን ሙቀት እያገኙ በመቆየታቸው ብቻ ድንጋዮቹ ጫጩቶች አይሆኑም። ምክንያቱም የደሮዋ ማቀፍና ሙቀት ወሳኝ ስላልሆነና ውጫዊም በመሆኑ ነው፡፡ ዋናው የእንቁላሉ ውስጣዊ ህይወት ወሳኝነትና የአካባቢ መመቻቸት ሚና ተደምሮ ነው ለውጡ የሚከሰተው።

የቀለም አብዮት ውድቀትም የሚጠነሰሰው ከውልደቱ ነው። ሲጀመር ሊብያዊ፣ ግብፃዊ፣ የመናዊ ወይም ኢትዮጵያዊ አይደለም። ከውጭ መጥቶ ውስጥን ማመስ ይችላል እንጂ መሰረታዊ ለውጥ ሊያመጣ አይችልም። እሳካሁንም ውጤት ሲያመጣም አልታየም። በዓለማችን በዚህ አብዮት/ለውጥ አንድም የተሳካ ለውጥ ያመጣ አገር ሊጠቀስ የሚችል የለም። እንዲያውም የቀለም አብዮት በተካሄደባቸው አገሮች በቀላሉ የማይድንና ረዥም ዘመን የሚቆይ ጠባሳ ቁስል ትቶ የሚሄድ አደገኛ ክስተት መሆኑ በተጨባጭ የተረጋገጠ ነው፡፡ ለዚህ ደሞ በተካሄደባቸው አገሮች ከድህረ ቀለም አብዮት በኃላ ያለውን ሁኔታ ማጤን በቂ ነው።

የቀለም አብዮት ባህርያት
የቀለም አብዮት አምስት አጠቃላይ ባህርያት የሚከተሉት ናቸው።
1.      የአንድ አገር ውስጣዊ ተጋላጭነት የሚጠቀም ነው።
2.      የሰብአዊና ዴሞክራሲ መብቶች ጥብቅና የቆመ መስሎ እና ሽፋን ተጠቅሞ ተፅእኖ መፍጠርና ጥቃት መፈፀም የሚችል ነው።
3.      በአገር ውስጥና በውጭ የተቀናጀ ዝግጅት ያደርጋል።
4.      አጋጣሚዎች በመጠቀም ወይም አጋጣሚዎችን ሆን ብሎ በመፍጠር አለማውን ለመፈፀም የሚተጋ ነው።
5.      ሆነ ተብለው በሚፈበረኩ ውሸቶችና ልብወለድ ትርክቶች ዜናዎች፣ ዘገባዎች፣ ጥናታዊ የሚመስሉ ሃተታዎች በመሰራትና በመንዛት ህውከትና ሽብር መፈጠር ነው።

የቀለም አብዮት ስልቶች
የቀለም አብዮት አንቀሳቃሽ ሐይሎች የተለያዩ ስልቶች እንደየአገሩ ሁኔታ የሚጠቀሙ ቢሆንም በአጠቃላይ ግን የሚከተሉት ስልቶችን እንደሚጠቀሙ መገንዘብ ይቻላል። 

1) የቀለም አብዮቱ በየምዕራፋ ተከፋፍሎ ብቃት ባለው ዝግጅትና ክትትል ይፈፅማሉ።
·         2) ዒላማ በተደረገው አገር የተቃውሞና የዓመፅ ሁኔታ/ድባብ እንዲነግስ ያደርጋሉ።
·         3) ከፍተኛ የሚድያ ዘመቻ በመክፈት ብጥብጥ ይጭራሉ።
·         4) በውስጥም አነጣጥሮ ተኳሾችና ቅጥረኞች ይጠቀማሉ። ይህ በቂ አይደለም ካሉም ሰብኣዊ ቀውስ ተፈጥሯል በሚል ሰብብ የልዕለ ሐያላኑ የራሳቸው ሐይል ወይም የጎረቤት አገር ሐይል ተጠቅመው ወረራም ይፈፅማሉ። በሂደትም በሰበብ አስባቡ አገሩን ያፈራርሳሉ።
·         5) የመንግስት ደጋፊ የሆኑ የአገር ውስጥ ይሁን የውጭ አካል ከህዝብ ለመነጠል ይሰራሉ።
·         6) ቅጥረኛና ተላላኪ መንግስት በመፍጠር ለማረጋገትን ለሟቋቋም በሚል ስም አገር ይዘርፋሉ።

እነዚህ ከላይ ያየናቸው ባህሪያትና ስልቶች የቀለም አብዮት በተካደባቸው አገሮች እንዴት ተግባር ላይ እንደዋሉና እንደተፈፀሙ በምሳሌነት ማየት ይቻላል። 

የቀለም አብዮት ሙከራዎችና ውጤቱ በኢትዮጵያ

የቅድመ ቀለም አብዮት ሁኔታ

በአገራችን የፋሽስት ደርግ ስርዓት በኢትዮጵያ ህዝቦች ትግልና መስዋእትነት በ1983 ግንቦት 20 ተገረሰሰ፡፡ ከሽግግሩ ወቅት ጀምሮም የመረጋጋት፣ የሰላም፣  የዴሞክራሲና የተስፋ ብርሃን መታየት ጀመረ። ያኔ ደርግ በአስገዳጅነት የመሰረተው ሰራዊት ወደ ሚልዮን የሚጠጋ ነበር። እዚህ ላይ በግልፅና በማያሻማ  መልኩ መገለፅ ያለበት ጉዳይ አለ፡፡ የደርግ ርዝራዦች በውዴታ ያላሰለፉትን፣ የህዝብን ጥያቄ ለመጨፍለቅ መሳርያ አድርገው የተጠቀሙበትንና ስልጣናቸው ለማራዘሚያ የሚዋጋ የግዳጅ ሰራዊትን  የደርግ ሰራዊት አትበሉ ይላሉ፡፡ ነገር ግን  በምን መለከያ የኢትዮጵያ ሰራዊት እንበለው ቢባሉ ብቁ መልስ የላቸውም። ሐውዜን ላይ በገበያ ቀንና በጠራራ ፀሓይ ህዝብን በአውሮፕላን ቦምብ የሚደበድብ የደርግን ሰራዊት ከማለት ውጭ የኢትዮጵያ ህዝብ ሰራዊት ነበር ብሎ ለሐውዜን ኢትዮጵያዊ ማሳመን እንዴት ይቻላል? ለኔ በፍፁም አይቻልም ነው፡፡

ድህረ ደርግ የኢትዮጵያ ሽግግር መንግስት የመራው ኢህአዴግ ጠላቱን እና ወዳጅን በደንብ ለይቶ ያውቅ ነበር፡፡ ደርግ በሐይል ከወላጆቻቸውና ከቤተሰቦቻቸው ቀምቶና አስገድዶ ወታደር ያደርጋቸውን እንደ ጠላቱ ያየበት ሁኔታ አልነበረም፡፡ ኢህአዴግ ወታደሮቹ እንደ ዜጎች ብቻ ሳይሆን እንደ ወዳጅ የህዝብ አካል በመውሰድ ወደ ሲቪልነት የሚቀየሩበትና መልሰው ኑሯቸውን የሚመሰርቱበት ዓላማ ይዞ ነበር የተንቀሳቀሰው፡፡ ይህንን ስራ የሚመራ መስርያ ቤት አደራጅቶ የተሃድሶ ስልጠና በመስጠት ወታደሮቹ በአጭር ጊዜ ራሳቸውን እንዲያቋቁሙ ማድረጉ በታሪክ የሚወሳ ብቻ ሳይሆን ለሌሎች አገሮችም ጥሩ ልምድና ተሞክሮ ሆኖ አገልግሏል።

ኢህአዴግ ከደርግ በኃላ የደርግን ፋሽስት መንግስት ያሸነፍኩት ወይም የአንበሳው ድርሻ ሚና የነበረኝ እኔ ነኝ ብሎ ስልጣን ለብቻየ አላለም፡፡ ደርግን በተለየ ዓላማ ቢሆንም አብሮት እንደ ተዋጋው የኢሳያሱ ሻዕብያ/የበኃላው ህግደፍ ስልጣንን ያለ ህዝቡ ምርጫ ብቻየ ልቆጣጠር አላለም። ኢህአዴግ ከሌሎች ድርጅቶች ጋር በመሆን አገሪትዋ በቻርተር በጋራ የሚያስተዳደሩበት ሁኔታ ፈጠረ። በህዝቡ ፍቃድ ላይ የተመሰረተ መንግስት ለመገንባት ደግሞ በወቅቱ በቻርተር አገሪቷን ሲያስተዳድሩ የነበሩት ድርጅቶች በጋራ የህገ መንግስት አርቃቂ ኮሚሽን አቋቋሙ። አቶ ክፍሌ ወዳጆም ኮሚሽኑን እንዲመሩ ተደረገ፡፡ አቶ ክፍሌ ኒውዮርክ ሆነው ደርግን ሲቃወሙ የነበሩ አገር ወዳድ ሙሁር ነበሩ። ኮሚሽኑም አንባቢና ዕድሜ ጠገቡ አቶ ክፍሌ እየመሩት ዘመናዊና ወቅታዊ፣ የኢትዮጵያ ሁኔታ መሰረት ያደርገና አለም አቅፍ ሕግጋትን ያከበረና የሚያኮራ የህገ መንግስት ማርቀቅ ስራ ሰራ። ህገ መንግስቱ ልሂቃን አወጡት ተብሎ ይፅደቅ አልተባለም። በገጠርም በከተማም ህዝቦች በየአካባቢው ጥልቅ ውይይትና ክርክር አደረጉ። በመጨረሻም ህዝቦቹ ተወካዮቻቸው በመላክ (ህገ መንግስቱ ሲፀድቅ ከኦሮሚያ ክልል ከባሌ ገጠር አካባቢ የመጡ ሙስሊም ሽማግሌ አባት በደስታ ሲዘሉ በተደጋጋሚ በቴሌቭዥን ተቀርፀው የሚታዩት ዓይነቶች ሳይቀሩ ተሳትፈው) ያፀደቁት ህገ መንግስት ፀደቀ።

ምርጫም በኢትዮጵያ ታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ተካሂዶ የተመረጠ መንግስት የሚያስተዳድር አካል በህዝቦች ፍቃድ በፌደራልም በክልሎችም ተመሰረተ። ህዝቦች ለመጀመርያ ጊዜ ራሳቸውን በወኪሎቻቸውና በአፍ መፍቻ ቋንቋቸው መተዳደር ጀመሩ። ዲሞክራሲ በተግባር ተጀመረ። የመደራጀት መብት፣ ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ መብትና የመፃፍ መብት በህዝብ ትግል ተረጋገጠ። ጋዜጦችና መፅሔቶች እንደአሸን ፈሉ። ኢትዮጵያ ዴሞክራሲ እየተጠቀሙ ዴሞክራሲ የለም ብለው መናገር፣ መፃፍና በአደባባይ መቃወም የሚቻልበት አገር ሆነች። የፋሽስትን ደርግ ታሪክ በአወንታ ለማቅረብ ጭምር የሚፈቅድ ስርዓት ተፈጠረ። ጀርመናዊያን  እሰከአሁን ድረስ የፋሽስት ሂትለር ናዚ ፓርቲ አባላትን የመደራጀት መብት አግደዋል። የናዚን የሂትለርን ስርዓት ማወደስ ጀርመኖች ከልክለዋል። ይሁን እንጂ አንድን ትውልድ ሙሉ የጨፈጨፈው የኮ/ል መንግስቱ ኢሰፓ ፓርቲ አባላትና የፋሽስት ደርግን ታሪክና የጨካኙ መሪ ታሪክ ማወደስ መደራጀት መብት የማይገድብ ዴሞክራሲ ኢትዮጵያ ላይ በህገ መንግስቱ እውን ሆነ። የኢሠፓ አባላት የነበሩ እነ ሃይሉ ሻውል፣ ሃይሉ አርአያ፣ ኢንጅነር ግዛቸውና፣ ደበበ እሸቱና መቶ አለቃ ሲሳይ አገኔ ተቃዋሚ ድርጅት ፈጥረው እንዳሻቸው የፈለጉትን ሃሳብ እየገለፁ ተደራጅተው በምርጫ ተወዳደሩ። የመሰላቸውን ተቃወሙ። መብት ያጎናፀፋቸውን ህገ መንግስት ሁሉ መተቸትና መቃወም ቻሉ።

ነግር ግን ምንም እንደማይባሉ ሲያቁ መብታቸውን ባለጉበት፡፡ከህግ ውጭ ህዝብን ከህዝብ የሚያጋጭ በህገ መንግስቱ የተከለከለውን በተግባር መጣስ ጀመሩ። በህግ ሲጠየቁ ጋዜጠኛ/ፖለቲከኛ ታሰረና ተጠየቀ ማለት ጀመሩ። በምርጫ ትተው በሁከት ከህዝቡ ድምፅ ውጭ ስልጣን እየተመኙ በህግም ከህግ ውጭም ካልተጫወትን በሚል ተንቀሳቀሱ። የተጀመረውን ሰላም፣ መረጋጋት፣ ዲሞክራሲ፣ ልማትና ዕድገት ለማንቋሸሽ ህግና ህገወጥነት እያጣቀሱ መሄዱን መረጡ።

በዚህ ወቅት አክራሪው የኒዮ ሌበራል ሐይል የኢትዮጵያን መንግስት የፖሊሲ ነፃነትና በራስ መተማመን (በሌላ አጠራር ለጌቶች ምክርና ትዕዛዝ ሳትቀንስ መቀበል ላይ የማይተጋው) በህዝብ የተመረጠው የኢህአዴግ መንግስት አልዋጥ ይላቸው ጀመር። አክራሪ ኒዮ ሌበራልስቶቹ እሱ ሲፈቅድ የሚተባበረን ሲቃወም ደግሞ ድህነታችን ይዘን ክብራችንና ሉዓላውነታችን እንመርጣለን የሚለውን ኢህአዴግ ማንበርከክ ወይም መጣል የሚል ግብ ይዘው ሙከራዎች ማድረግ ጀመሩ። አክራሪዎቹ ኒዮ ሌበራሎች ኢህአዴግን መንቻካ የሚል ስም አውጥተውለት ነበር፡፡ የሰራቸው በጎ ተግባራትም የማያሞጉሱት በዚህ ቅሬታቸው እንደሆነም ይታወቃል፡፡

ይህም ሆኖ የኢትዮጵያ መንግስት አክራሪ ካልሆኑት ሌበራል የምዕራብ አገራት መንግስታት አመራር በመተባበር ከልብ የሚሰራቸው ስራዎች ነበሩ፡፡ ለምሳሌ በትምህርት፣ በጤና፣ በድህነት ቅነሳ፣ በዲሞክራሲ፣ በፀጥታና ድህንነት ስራዎችና ሌሎች በሚያደርጋቸው እንቅስቃሴዎች በመንግስታቱ ምስጋና እየተቸረው ነበረ። የሚያበረታታ ድጋፍም ይደረግለት ነበር። በኢትዮጵያ መንግስት በወቅቱ የነበረ የውስጥ ስራ ስኬታማ መሆኑ ተያይዞ የውጭ ስራውም ስኬታማ በመኖሩ ትብብሩ ወደ ላቀ ደረጃ ደርሶ ነበር። በኢትዮጵያ ታሪክ ታይቶ በማይታወቅ ደረጃ የሁሉም የምዕራብ አገሮች መሪዎች ኢትዮጵያን የሚጎቡኝበት ሁኔታ ተፈጠረ። የምስራቁ ዓለም መሪዎቹም በተመሳሳይ የሚጎበኟት አገር ኢትዮጵያ ሆነች። በመሆኑም አክራሪዎቹ ኒዮ ሊበራሎች የተመቻቸ ሁኔታ ሳያገኙ ቀሩ። ሙከራቸውን ግን አላቋረጡም ነበር።

የ1997 ምርጫ ወቅት ያልተሳካና ስም ያልወጣለት የቀለም አብዮት ሙከራ
ብዙ ጊዜ የቀለም አብዮት ሲካሄድ ወይም ከተካሄደ በኃላ ስም ይወጣላቸዋል። በአገራችን ኢትዮጵያ የ1997 ዓ/ም የቀለም አብዮት ሙከራ መጠርያ የቀለምም ይሁን የወቅት ወይም በሌላ መንገድ ስም አልወጣለትም።

ሙከራው የተደረገውም የከሸፈውም ምክንያት በህዝብ ተመርጦ ሲያስተዳድር በቆየው ኢህአዴግ ውስጣዊ ሁኔታ ጋር የተያያዘ ነው። ሙከራው የተደረገው በኢህአዴግ ውስጥ በነበረው ድክመት ምክንያት ምቹ ሁኔታ በመፈጠሩ ነበር። ሙከራውም የከሸፈውም ኢህአዴግ ድክመትም ቢኖረውም ለማረምም ዝግጁነትና ብቃትም ስለነበረው ነበር፡፡ በውቅቱ የውስጥ ችግሩን በራሱ ፈቶ ህዝቡን ለማገልገል ቁርጠኛም ስለነበረና ህብረተሰባዊ መሰረቱም ጠንካራ ስለነበረ ተንገዳገዶ ትምህርት ወሰደበት እንጂ ሊወድቅ አልቻለም።

የያኔው የቀለም አብዮት በአዲስ አበባና በአማራ ክልል ከተሞች ካልሆነ በስተቀር ከዛ ያለፈ ስፋት አልነበረውም። ሆኖም ግን ዘረኛና የኢንተርሃሞይ ባህሪ የነበራቸው መፈክሮችን አንግቦ የመንግስት ስልጣንን ህገ መንግስታዊ ባልሆነ ነውጥና ግርግር ፈጥሮ ለመቆጣጠር ወይም ለመካፈል ዓላማ ያደረገ ነበር፡፡ ለዚህም የወጣቶች ሞት አቅዶና አስልቶ፡፡ ይህን ያህል ወጣቶች አስገድለን ስልጣን በሐይል ቀምተን እንይዛለን የሚል ፍልስፍናና ዕቅድ የነበረው ያልተሳካ ቀለም አብዮት ነበር። የቀለም አብዮቱ ባለቤቶች ይህን ወደ አገራችን የላኩት አብዮት (exported revolution) ቢከሽፍባቸውም አክራሪ ኒዮ ሌበራሊስቶቹና ተላላኪዎቻቸውም ትምህርት ያገኙበትና በቀጣይ ለሚሰሩት ቀለም አብዮት ዕቅድ ልምድ የገበዩበት ሙከራ ነበር።

የ2007 - 2010 ዓ/ም የመደመር ቀለም አብዮት
ኢህአዴግ ከ1997 ዓ/ም የቀለም አብዮት ሙከራ ከፈፃሚዎቹ በላይ ውስጡን ፈትሾ ትምህርትና ልምድ አግኝቶ ነበር፡፡ ለተፈጠረው የውስጥ ችግር መፍትሔው ውስጣዊ ጥንካሬውን መጠበቅ እንዳለበት ተገንዝቦ ነበር፡፡ የህዝብ ወገንተኝነቱን ማጠናከር፣ ለህዝብ የገባውን ቃል ማክበርና ህዝብን እያዳመጠ የህዝብን ጥያቄና ፍላጎት መመለስና ሟሟላት እንዳለበት ተረዳ፡፡ መሰረታዊ መፍትሔውም ፈጣን ዕድገት ማምጣትና ድህነትን በከፍተኛ ደረጃ መቀነስና ብሎም ማጥፋት መሆኑን ተገንዝቦ በመስራቱ በተከታታይ ተዓምራዊ የሆነ ለውጥ ማስመዝገብ የቻለበት ሁኔታ ተፈጠረ። ኢህአዴግም በህዝብ ዘንድ ተቀባይነቱ በከፍተኛ ደረጃ ጨመረ።

ለቀለም አብዮት የማይመች ሁኔታ ተፈጥሮ አገራዊ ምርጫዎች ሰላማዊ፣ ነፃና ፍትሓዊ በሆነ መንገድ መፈፀም ተቻለ። ተቃዋሚዎች በ1997 ዓ/ም ምርጫ ተመርጠው ሲያበቁ ለመረጣቸው ህዝብ ክብር ስላልነበራቸውና ከሁኔታው ጋር መሄድ ስላልቻሉ ፓርላማ አንገባም አሉ፡፡ ይህ በማለታቸው ቀጥለው በነበሩ ምርጫዎች ሊመርጣቸው የሚፈልግ የህብረተሰብ ክፍልም ሊያምናቸው ባለመቻሉ የፈለጉትን ድምፅ ሳያገኙ ቀሩ። እንዴት መቶ በመቶ ኢህአዴግ አሸነፈ ብለው ከመጮህ ውጭ የራሳቸውን ጉድለት ማየት ተሳናቸው። ከኢህአዴግ ውጭ በሶማሊ፣ በአፋር፣ በሀረሬ፣ በቤንሻንጉል ጉሙዝ እና በጋምቤላ ያሉ ፓርትዎች ያሸነፉትንም ጨምረው ኢህአዴግ መቶ ፐርሰንት አሸነፈ ብለው እስከ 2007 ዓ/ም ሲወቅሱና ሲያለቃቁስበት ቆዩ። በተቀራኒው ደሞ ኢህአዴግ በምርጫ ብቻ ሳይሆን በልማት በዕድገትም ድል ላይ ድል እየተጉናፀፈ ሁለገብ ፈጣን ለውጥ እያስመዘገበ ቀጠለ።

ድል ሲበዛ እርካታ የሚባል አደገኛ በሽታ በኢህአዴግ ውስጥ ተፈጠረ፡፡ ከፍተኛ አመራሩ ከህዝባዊ መስመሩ እየወጣ ሄደ፡፡ ስልጣንን ለህዝብ ማገልገያነት መጠቀም እየተወ የራሱ የግል ፍላጎት መጠቀሚያ አድርጎ የሚያስብ አስተሳሰብ በአመራሩ ውስጥ እያደገ መጣ። ይህን አዝማሚያ ለመታገል የተደረጉ ሙከራዎች አዝማሚያውና እርካታው እየተደጋገፉ የውስጥ ትግሉን ሙከራ አደናቀፉት። የውስጥ ትግል ሙከራዎቹ በተደጋጋሚ ከሸፉ። ኢህአዴግ በውስጡ የነበረውን በሽታ ፈጥኖ ለማከም በማቅማማቱና ጊዜ በመውሰዱ ለቀለም አብዮት የተመቻቻ ሁኔታ ፈጠረ። የአክራሪ ኒዮ ሊበራሎቹ የቀለም አብዮት ዕቅድ እስከ 2012 ዓ/ም  የኢህአዴግን የመተካካትንም ፕሮግራም ግምት አስገብቶ የወጣ ዕቅድ የነበረ ቢሆንም በውስጥ በሽታው የተዳከመዉ  ኢህአዴግ ቀድሞ ፍርክስክሱ ወጣ፡፡  ቀድሞ የቀለም አብዮት ዕቅድ መፈፀም ጀመረ።

ኢህአዴግ በስልጣን ጥመኞችና ለውጭ ሐይሎች ባደሩ የራሱ መስለው በውስጥ በነበሩ የውስጥ የቀለም አብየቶኞች ፍርክስክሱ አወጡት፡፡ በፓርቲ ውስጥ በህቡእ በተቀናጀና በውጭም በህዝብ ስም በተደራጁና በተዘጋጁ የቀለም አብየተኞችም ጭምር የህዝቡና የወጣቱን እውነተኛ ጥያቄና ትግል ጠልፈውና ዓላማውን አዛብተው የራሱን ህጋዊ የተመረጠ መንግስት በቀለም አብዮተኞቹ እንዲነጠቅ የተመቻቸ ሁኔታ ፈጠሩ። በተጨማሪም ከፓርቲው ውጭ የአክራሪው ኒዮ ሊበራል ቅጥረኞችና የሶሽል ሚድያ ቀለም አብዮተኞች እነ ጁሓር፣ ስዩም ተሾመና ሌሎችንም በስራቸው አደራጅተው ተንቀሳቅሰዋል፡፡ የግብፅ መከላከያ በኢትዮጵያ ላይ ያዘጋጀውን ቢግ ዳታና አርቲፊሻል ኢንተሊጀንስ ቴክኖሎጂ (BD and IA) አቅም ተጠቅመው የውሸት ዜናቸውን (fake news) የሌላቸውን አቅም ፈጥሮ በከፍተኛ ደረጃ በማባዛት በሚስኪን ህዝቦች ላይ የውሸት ተስፋና ጉጉት ፈጠሩ፡፡ በሁለንታዊና በፈጣን ለውጥ ዓለምን ያስደነቀ ስኬት ያረጋገጠውን በአብዮታዊ ዲሞክራሲ የተመራውን ግዙፉን ኢህአዴግ በራሱ በሽታ እየከሳ በመምጣቱም በቀላሉ ማንገዳገድ ቻሉ። ጊዜ በማይሰጥ ሁኔታ አጣደፉት። ኢህአዴግ በዋናነት በራሱ የእርካታ ተህዋስ የፓለቲካ አተት ያዘው፡፡ 

የመደመር ቀለም አብዮተኞቹ ትልቁ ስትራተጂ ለሁሉም ነገር ተጠያቂው ከፍተኛ መስዋዕትነት ከፍሎ ደርግን የተፋለመውና ህገ መንግስታዊ ስርዓት እውን እንዲሆን ከሌሎች ህዝቦች ጎን ተሰልፎ የታገለውን የትግራይ ህዝብና መሪው ድርጅቱ ህወሓት አደረጉ፡፡ ህወሓት በወቅቱ 2010ዓ/ም ለሳላሳ አምስት ቀናት ስብሰባ አድርጎ ራሱን ፈትሾ ከበሽታው ለመዳን ውስጣዊ ትግል በማድረግ ለመታረም ዝግጁ ሆነ። በሌላ በኩል ደግሞ ይህን በጥልቀት ተሃድሶ ራሱን ለመለወጥ ዝግጁ የሆነውን ህወሓት ላይ ያነጣጠረ ዘመቻ ለማድረግ የራሱ የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች ኦሮማራ የተባለ የጥፋት ቅንጅት ፈጥረውና ተደምረው ማጥቃት ጀመሩ። ይህ ዘረኛና ፀረ አብዮታዊ ዲሞክራሲ መስመር የሆነ የጥፋት ስትራተጂ ዓላማ ያደረገው ልማታዊውን የኢህአዴግን መንግስት ገርስሶ መጣልና አሻንጉሊት ተላላኪ መንግስት መፍጠር ነው። ይህም ጥልቅ ተሃድሶ በማካሄዱ ምክንያትና ቀድሞ መዳን የሚችለውን ህወሓትን አስቀድሞ ለመምታት ነው የኦሮማራ የስትራተጂው እምብርት።

ስትራተጂውን ለማሳካት አክራሪው ኒዮ ሊበራል ሐይል አክራሪ ዲያስፖራና አገርቤት ያሉትን ቅጥረኞች ብቻ አይደለም የተጠቀመው። ግብፆች፣ ኤርትራና በኃላም ሌሎች የአረብ አገሮችም ኃይል ተጠቅመዋል። መጨረሻውም በተዳከመውና አንድነት ባልነበረው ጥልቅ ተሃድሶ አደርጋለሁ ብሎ ሳያደርግ በቆየው ኢህአዴግ ምክርቤት ስብሰባ በኦሮማራ አደረጃጀትና በገንዘብና ቃል ተገብቶላቸው በተሰበኩ ተሰብሳቢዎች የምርጫ ድራማ ተደረገ። የሸፍጥ ምርጫ በታቀደው መሰረት በውስጠ ፓርቲ መፈንቅለ መንግስት ተካሂዶ ኮ/ል አብይ ተመረጡ። ወዲያውኑ በለሊቱ ጥቁሩ ፕሮፖጋንዳ ስራም ተጀመረ።

በመቀጠልም የመደመር ቀለም ሪፎርም/አብዮት በፌደራል ደረጃ ስልጣን በብቃት ለመቆጣጠር ዝርዝር ዕቅድ ተሰጥቶት በሊስቱ መሰረት ከህግ ውጭም ውሳኔ እየተወሰነ የቀለም አብየቱ እንዳይቀለበስ ፈጣን የሆኑ እርምጃዎች ተወሰዱ። ብዙ ሰዎች አብይ በራሱ ጭንቅላት እርምጃዎቹን የፈፀማቸው ይመስላቸዋል። እንዲመስላቸውም የግብፁ ቢግ ዳታና አርቲፊሻል እንተሊጀንስ ቴክኖሎጂ (BD and IA) ከፍተኛ ሚናውን ተጫውቷል። አብይም ጥሩ ፈፃሚ ባይሆንም አድርግ የተባለውን በተዋጣለት መንገድ ይተውነዋል። የተዋጣለት ቀለም አብዮተኛ አይደለ? አብይ ፊቱንም በሜክአፕ ቀለም አስውቦና በአለባበስ ሽክ ብሎ ትልቅ ለውጥ ያደረገ ያስመስለዋል።

የትላንት ታሪክን ጠባሳ የነበረም ያልነበረም ብቻ አጋግሎ በማቅረብ እሱ መሲሕ መጥቶ እንደፈታው ይመፃደቃል። የራሱ ስህተትም የኔ አይደለም የትናንት ቁርሾ ነው ብሎ ያላክካል። ቦንብ ከመቶ ሜትር በላይ ርቀት ባለው ስፍራ ተወርውሮ እኔን የለውጥ ሃዋርያ ለመግደል ተሞከረ ብሎ ያለቃቅሳል።  ራሱ የፈጠረው ድራማ ነው ተብሎም ይታማል። በሚያሰለች ሁኔታ ይደጋግመዋል። ነገር ግን በኢትዮጵያ ህዝብ ልብ ውስጥ የሰፈረው ተወዳጁ እንጂነር ስመኘው በጠራራ ፀሓይ ተገድሎ እንኳን ሊደጋግመው ራስ ወዳዱ ጠቅላይ ሚኒስተር ተብዬ ምንም ሃዜኔታ አላሳየም። እሱ ግን አንዴ የመግደል ሙከራ ተደረገብኝ አንዴ የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ ተደረገብኝ ብሎ ያዙኝ ልቀቁኝ ይላል። እውነት እንነጋገር ከተባለ አንድ ሰው ቦምብ ቢወረውር ከሳላሳ ሜትር በላይ አርቆ መወርወር አይችልም። ከዛም ጉዳት የሚያደርሰው በሜትርና በሁለት ሜትር ራድያስ ውስጥ እንጂ እንደሚሳይል እየተምዘገዘ ክብር ትሪቡን ድረስ ሄዶ የቀለም አብዮተኛ መሪን አይገድልም ወይም አይስትም። ወታደር ነኝ የሚሉት መሪ ዩኒፎርም ብቻ መልበስ ብቻውን ወታደር ያሰኛል እንዴ? ያስብላል፡፡ የሆሊውድ ፊልም ተዋናይ እንኳን ዩኒፎርም ብቻ ለብሶ አይተውንም። ትንሽ ወታደራዊ ዕውቀት እንዲኖረው ይደረጋል እንጂ። ታድያ በምን ተዓምር ነው በዛ ርቀት የመግደል ሙከራ ተደረገብኝ የሚሉት? ሳይጣራ ከመቅፅበት የደመደሙት?  ለኢንጅነር ስመኘው አገዳደል በዛው ፍጥነት ለምን ድምዳሚያቸውን አልገለፁልንም ታድያ? በውሸት የተገኘ ስልጣን በውሸት ዕድሜ ለመግዛት ነው።

የቀለም አብዮት ዕቅድና ስራ በሦስት ምዕራፍ ይከፈላል። ቅድመ አብዮት፣ በአብዮቱ ወቅትና ድህረ አብዮት ምዕራፋት አሉት።

በኢትዮጵያ የመደመር ቀለም አብዮት ሁለቱ ምዕራፋች ተፈፅመዋል።ኮ/ል አብይ ሁለቱም ምዕራፎች በድል ተወጥተዋቸዋል። ሦስተኛ ምዕራፍ የድህረ መደመር ቀለም አብየቱ ምእራፍ ኮ/ል አብይ ምን እያሉና እያደረጉ  ነው? አብይ ስልጣን ከያዙ በኃላ ልገደል ነበር አሉ፡፡ መፈንቅለ መንግስት በአብንና በባልደራስና ከባህርዳር ተጠነሰሰብኝ አሉ፡፡ የዳውድ ኢብሳን ኦነግንም ይከሳሉ። ከዚህ ሁሉ ጀርባ ደግሞ ለውጡን ያልተቀበለው የትግራይ ህዝብና ህወሓት ተጠያቂ  ያደርጋሉ። ሚድያዎችን በብር አፍነው የትላንት ሌባና ሰብኣዊ ጥሰት ተጠያቂ፣ አሁኑም የራሳቸው ዓቅም ማነስ ጭምርና ፀረ ህዝብ ውሳኔ በመወሰን የሚፈጠሩትን ችግሮች ሁሉንም ህወሓትና የትግራይ ህዝብ ላይ ያላክካሉ። ይከሳሉ። የትግራይ ተወላጆች ብቻ በመሆናቸው ሰዎች ያስራሉ። ይባስ ብሎም ከትግራይ ተወላጆች ጋር ሰርታቹሃል ተብለው ያለምንም ጥፋትና ማስረጃ ሰዎች ያስራሉ። ፍርድ ቤት ማስረጃ የላችሁም ዋስትና ይሰጣቸውና ውጭ ሁነው ይከራከሩ ያላቸውን የፖለቲካ እስረኞች የፍርድ ቤትን ስልጣን ተጋፍተው እስሩን ያስረዝማሉ። በረከትንና ታደሰ ጥንቅሹን ውቃቤያቸው የኮ/ል አብይ መንግስት መሪነትን አልወደደውም ብለው በኦሮማራ ኔትዎርክ ዘብጥያ ያወርዳሉ። ታድያ ይህ ድንቄም ለውጥ አያሰኝም።

በአገር ውስጥ ከሶስት ሚልዮን በላይ ህዝብ በማፈናቀል ዓለምንም ሶርያንም ያስናቅን እንዲንሆን ያደረገን፤ ህገ መንግስታዊ ያልሆነ በኢትዮጵያ ህዝቦች ምክርቤት ያልፀደቀ አስቸኻይ ጊዜ አዋጅ በኦሮሚያ፣ በሶማሊያ፣ በአማራ፣ በቤንሻንጉልና በቅርቡም በደቡብ ህዝቦች ክልሎች ያወጀለን፤ የአንድነት መንፈስ የጠፋበት፣ የሰላም ሁኔታ የሌለበት፣ ስጋትና ጥርጣሬ የሰፈነበትና ተስፋ የጨለመበት ህዝብና አገር እንድንሆን ያደረገንና ሌሎችም የቀለም አብዮቱ ቱሩፋት እንድንቋደስ ያደረገን የቀለም አብዮት መሪ የአብይ አመራር ውጤት አይደለምን?

በጠራራ ፀሓይ ባህርዳር ላይ የህዝብ ተመራጮች የሆኑ የክልል መሪዎችን ከስልጣኔ ልታወርዱኝ እየወሰናቹህ ነው ብሎ በመስርያ ቤታቸው የሚረሽን ጋጠወጥ ያለበት አገር ፈጠሩ። በዛኑ ቀን በአዲስ አበባም የመከላከያ ኤታማዦር ሹም ከወዳጃቸው ጀነራል ጋር በቀላሉ ተገድለው ስንት የጀግንነት ታሪክ ያሳለፉ ከፍተኛ መኮነኖች አገሪቱ እንድታጣ ሆነ። አብይ የአዞ እንባ አነባ። ምንም ሳያጣራ መፈንቅለ መንግስት አለ። ምርመራ ግን የለም። እንሆ እንጂነር ስመኘው መቶ ቀረ። እነ ዶ/ር አምባቸው እና አነ ጀነራል ሰዓረም ሞተው ሊቀሩ ነው? ቤተሰብና ወዳጅ ከማልቀስ ውጭ ምንም ማድረግ አልቻለም፡፡አሁንም እየተረሱ ነው ማለት ነው?

አብይ አህመድ ከግድያው ንፁህ እንዳልሆኑ አሁንም ስማቸው ይነሳል፡፡ ተወዳጁ ስመኘው አስገድለውታል እንደሚባሉት ሁሉ አሁንም አየታሙ ነው። ኮነሬሉ ለምርመራው ሳይሆን የሚጨነቁት ለራሳቸው ስልጣን ነው። ነገር ግን ቢያንስ በቀጥታ ግድያው ላይ ተሳትፎ ባያደርጉም ከተጠያቂነት አያመልጡም። ሁኔታው የአስተዳደራቸው ጉድለት ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ነው።አየር መንገዳችን ቴሌኮሚኒከሽን ምድር ባቡር ወዘተ ሊቸበችቡት ሲሯራጡ እያየን ነው።ኢህአዴግን አፈራርሰው ከጨረሱ በኃላ አሁን ደግሞ ውህደት ሊፈፅም ነው ብለው ብቻቸውን ወስነው እየተጣደፉ ነው።ይህ መጣደፍ ደግሞ በኢኮኖሚም በአመራርም ለከፍተኛ ውድቀት የሚዳርገን ነው።

በአጠቃላይ በአገራችን እያጋጠሙ ያሉ አስከፊ ክስተቶች የጋጠወጡ መሪ ኮ/ል አብይ አህመድ አመራር ውድቀት ውጤቶች ናቸው። ስልጣኔን ብቻ ብሎ የሙጥኝ የሚል መሪ የስራ ውጤት ከልማት ይልቅ ጥፋት፣ ከሰላም ይልቅ ሁከት፣ ከተስፋ ይልቅ ስጋት ላይ የምንኖርበት ሁኔታ ተፈጥሮ አገራችን ኢትዮጵያ በፍጥነት ወደ መበታተን መፍረስ አደጋ እየተቃረበች ነው።


አገራችን ኢትዮጵያ ልንታደጋት የምንችለዉም ሁላችንም ነን፡፡ በቅርቡ አገር ወዳዶች እንዴት አገራችን እናድናት ብለው በመቀሌ በህወሓት ተነሳሽነት የመጀመርያ ስብሰባቸውን አድርገዋል። ይሁን እንጂ በመደመር ቀለም አብዮተኞቹ ይህ ዓይነት ስብሰባ በበጎ አልታየም። እንደ መዳፈርም ተወስዷል። ህወሓትና የትግራይ ህዝብ የመደመር ቀለም አብዮቱን አለመቀበሉ ምክንያት አድርገው ውስጥ ውስጡ ሴራዎች ሲጠነሰሱበት ቢቆይም አልበገር ብሎ እየታገለ ይገኛል፡፡ አሁን በቅርቡ ያደረገውን ተነሳሽነትም በቀለም አብዮተኞቹ ጉዳዩን አሳሳቢ አድርጎታል።

የስልጣን ጉዳይ የሞት ሽረት ጉዳይ ሁነባቸዋል። አክራሪ ኒዮ ሊበራሎችም የነደፉት የቀለም አብዮት በተሟላ ውጤታማ እንዳልሆነ ቆይተው ቢሆንም ደርሰውበታል። በትግራይ ህዝብና በህወሓት መካከል ይፈጠራል ብለው የገመቱት ልዩነትና መቃቃር ሳይፈጠር በተቃራኒው ጠንካራ አንድነትና መግባባት በተለየም በአካባቢው ሰላምና መረጋጋት መስፈኑ ያልጠበቁት ነበር። አሁን እንደገና እያሳሳብዋቸው ያሉት ሁለት ነገሮች ናቸው። አንደኛ የኮ/ል አብይ መንግስት የቀለም አብዮት መክሸፍና ውደቀት ነው። ሁለተኛውና በነሱ ዓይን አደገኛው የህወሓትና የሌሎች አገር ወዳድ ድርጅቶችና ሰዎች በመተባበር አገሪቱን አድነው ያለውን ህገመንግስትና ፌደራሊዝም እንዳይታደጉትና ህገመንግስቱ ማሻሻል ቢያስፈልግም በራሳቸውና በህዝቡ ፍላጎት እንጂ በውጭ ሐይሎች አይሆንም ብለው እንቅስቃሴ መጀመራቸውን ነው።ይህንም ለመቀልበስ ብሎም አብይ አህመድና የመደመር ቀለም አብዮቱን ለማዳን አክራሪ ኒዮ ለበራሎቹ አሁንም አልተኙም። 


ለአንዴና ለመጨረሻ የቀለም አብዮት ሙከራ

በኢትዮጵያ በተካሄደው የቀለም አብዮትየአገር ውስጥም የውጭም ሁሉም ሐይሎች የተሳካና አስተማማኝ የስርዓት ለውጥ (regime change) ተረጋግጧል ብለው ተማምነው እንደነበረ ይታወቃል። በሁሉም የሚድያ አውታሮቻቸው አስረግጠው የገለፁት ይህንን ነበር። ኢሳያስ አፈወርቂ ከአስመራ game over ሲል፣ እነ ደመቀ መኮነንና ገዱ ከባህርዳር የጨለማ ዘመን አከተመ ብለው ሲያውጁ፣ አብይ አህመድ ከአዲስ አበባ የቀን ጅቦች ሲል ሁሉም የቀለም አብዮቶኞች ደስታና ፈንጠዝያ አስኩሯቸው ነበር። ህወሓት ላይመለስ ጨፍልቀነዋል አሉ። ከአሁን በኃላ ዲሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት፣ የብሄር ብሄረሰቦች መብት፣ ፌደራሊዝም፣ አብዮታዊ ልማታዊ ዲሞክራሲ፣ . . . ቅብርጥሴ ቅብርጥስጥሴ ብሎ ነገር የለም አሉ። ለሁሉም ነገር ለውጥ ላይ ነን፣ ሽግግር ላይ ነን ተባለ። ከየት ወዴት መሆኑ የማይታወቅ ጉዞ ለውጥ ተብሎ ተለፈፈ።

ነፃ ሚድያ የተባሉትም ይህን ቅኝት ብቻ ይዘው ተረባረቡ። Ltv፣ EBC፣ ዋልታ፣ ፋና፣ ናሁ፣ OBN፣ OMN እና ኢሣት በትግራይ ህዝብ፣ በህወሓትና እንዲሁም የትግራይ ህዝብና ድርጅት ዓላማ ደግፈው የቆሙት የሌሎች ህዝቦች አባላትም ሳይቀሩ ስም እየጠሩ ስም የማጥፋት ዘመቻቸውን አፋፋሙ። ጥሩ ስም ያስመዘገቡ በህዝባዊነታቸው በኢትዮጵያ ህዝቦች የሚከበሩና የሚታመኑ ተቃማትን እንዲፈርሱ በጥቁር ፕሮፖጋንዳ ዘመቱባቸው። በድህንነት፣ በፌደራል ፖሊስ ብሎም በመከላከያ ሰራዊት ላይ ምላሳቸውን ዘልዝለው ማስረጃ የሌለው ውሸት ደረደሩ።

የመደመር ቀለም አብዮተኞች ለውጭ መንግስታት እነዚህን መስራያ ቤቶች ገብተው ያሻቸውን እንዲያደርጉ በሩን ከፍተው እንዲገቡ ፈቀዱላቸው። የአገራችን ሉዕላዊነት በደንበር ሳይሆን በአገሪቱ እንብርት ውስጥ ተጣሰ። ለኢትዮጵያ አገራቸው ቀን ከለሊት ሲሰሩ የነበሩ የነዚህ ተቀማት አመራሮችና አባላት በሽብርተኞች፣ በአክራሪዎችና በውጭ አገር ሰላዮች ጥቆማ እየተደረገባቸው ለእስር ተዳረጉ። እንደነ ኢንጅነር ስመኘው፣ ጀነራል ሰዓረ፣ ጀነራል ገዛኢ፣ አቶ አምባቸው፣ አቶ እዘዝ፣ አቶ ምግባሩና ሌሎች የመንግስት አባላት፣ መኮንኖችና ወታዳሮች ደግሞ እየገደሉና እያስገደሉ እኛ አላየንም ብለው መልሰው ምርመራ ላይ ነን ይሉናል የነውጡ መሪዎች።

ለውጡ እየዋለ እያደረ ወደ ዋናው ባህሪው ወደ ነውጥነት ነው የተሸጋገረው፡፡ በሁሉም አካባቢ ሰላም ጠፍቶ ግጭት፣ ህውከት፣ ግርግር፣ ሞት፣ በሚልዮኖች መፈናቀል እና ከቦታ ቦታ መዘዋወር የማይቻልበት አገር ተፈጥሮ በኮማንድ ፖስት መተዳደር ከጀመርን ወራቶች እየተቀጠሩ ናቸው፡፡ ይህ አስቸካይ ጊዜ አዋጅ ህገ መንግስታዊ ያልሆነ በፓርላማ፣ በሚኒስተሮች ምክርቤት፣ ይሁን በኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚም የማይታወቅና ይሁንታ ያላገኘ ከጠቅላይ ሚኒስተሩም በደብዳቤም ያልተገለፀ በስልክና በስብሰባ ቀጭን የቃል ትዕዛዝ ተግባራዊ እየሆነ ያለ ነው። ይሁን እንጂ ይህ ህገወጥ አካሄድም ያሰገኘው ፋየዳ የለም፡፡ ህዝቡ ስለ ራሱ፣ ስለ አገር ድህንነትና ስለ ሰላም በቅድሚያ የሚጨነቅበት አዲስና ቅድሚያ የሚሰጠው ሁኔታ ላይ ይገኛል። አገር ልትፈርስ ገደል ጫፍ የደረሰችበት ሁኔታ ላይ ሁኖ ነገ ምን ሊፈጠር እንደሚችልና ወዴት እየተጓዝን እንደሆነ ማንም መገመት የማይቻልበት ሁኔታ ላይ እንገኛለን።

በሌላ በኩል የመደመር ቀለም አብዮት ዋና ዒላማ የነበረው የትግራይ ህዝብና መሪ ድርጅቱ በቀለም አብዮቱ ጎርፍ ለመጠራረግ ቢፈለግም አልተሳካም። ከስም ማጥፋት ጀምሮ እስከ የማፈናቀል፣ የማሰርና የመግደል   ጥቃት ደርሶበታል። አዲስ ትርክት ፈጥረው ጥቁር ቀለም እየቀቡ ሌላው ወንድም ህዝብ በትግራይ ህዝብና በመሪ ድርጅቱ የነበረው ፍቅርና ክብር ለመፋቅ ባለ በሌለ አቅማቸው ሰርተዋል። የነበረው አስተዳደር በህወሓት የበላይነት ይመራ እንደነበር፡፡ የኢትዮጵያን ህዝብ ሀብት ዘርፈው ወደ ትግራይ እንደወሰዱ። ሰብኣዊ ጥሰት በሌላው ህዝብ መፈፀማቸው። ፌደራሊዝም የተባለ ዘረኛ ስርዓት ፈጥረው የኢትዮጵያን አንድነት ማዳከማቸው። ሲጀመር የአማራ ህዝብ ጠላት ብለው ፈርጀው ወደ ትጥቅ ትግል ወጡ ብለውና ብዙ ሌሎች ልበወለድ የስም ማጥፋት ዘመቻ ሲያደርጉ ያለመታከት በአንድ አካባቢ በሰፈረ ህዝብ ፋሽስት ደርግ ለመገርሰስ ከፍተኛ መስዋእትነት መክፈል ብቻ ሳይሆን በምንም መመዘኛ ያልተመጣጠነ ሰብኣዊና ሀብት ኪሳራ የደረሰበትን የትግራይ ህዝብና ትግሉን በከፍተኛ ጀግንነት የመራ ድርጅትን ህወሓት ላይ ሲያነጣጥሩ ቆይቷል፣ እስካሁን ድረስም እየቀጠሉበት ነው።

አሁን ደግሞ ቢቀጠቅጡት መሞት ያልቻለው ህዝብና መሪ ድርጅቱ ህወሓት ለአንዴና ለመጨረሻ ለመምታት አዲስ ሴራ እየተሸረበ ነው። የመደመር ቀለም አብዮት በከፊል ደረጃ በአገር ደረጃ ቢሳካም በሰሜን የአገሪቱ ክፍል በሚፈለገውና በታሰበው መንገድ አልተሳካም ብለው በቅርቡ ገምግመዋል። የመደመር ቀለም አብዮት ቀያሶቹ አክራሪው ኒዮሌበራል ሐይሎች ይህ ግምገማ ቀድመው ቢደርሱም፣ በአገር ውስጥ አስፈፃሚ ያደረጉት አብይ አህመድ ግዴላችሁም እሰራላቸዋለሁ፣ እናሳያቹሃለን ጠብቁን ብሎና ኢሳያስ አፈወርቅም game over ብለው አሳስቷቸው ነበር። ይሁን እንጂ እቅዱ ባለመሳካቱ ምክንያት እንደ አዲስ ህወሓትን በመምታት ያታጋዩ ህዝብ ቅስም ለመስበር አዲስ ዕቅድ አውጥተው ዝግጅታቸውን ጀማምረዋል። በሌላ በኩል ተዳክሟል የተባለው ህወሓት ጭራሽ ተጠናክሮ የህዝብ ከፍተኛ ድጋፍ አግኝቶ በተለየ መንገድ በአካባቢው ሰላምና መረጋጋት ማረጋገጥ መቻሉና ብሎም ለሌሎች ህዝቦች ተስፋና ደጀን ሆኖ ማገልገል መጀመሩ ክፉኛ አስደንግጧቸው የቀለም አብዮት በትግራይ ደረጃ ለመፈፀም በሚልዮኖች ዶላር መድበው እንቅስቃሴ ጀምረዋል።

የመደመር ቀለም አብዮቱ መሪዎች ማን ናቸው?
ከውጭ ሃይሎች ዋናው የአክራሪ ኒዮ ሊበራሎች የሚመሩት የግብፅና ኤርትራ መንግስታትም ይገኙበታል። ከአገር ውስጥ ደግሞ ተላላኪዎቻቸው የሆኑት የመደመር ቀለም አብዮት መሪው አብይ አህመድና የግንቦት ሰባት/አዜማ እና የትግራይ ባንዳዎች ናቸው።

ዓላማው ምንድነው ነው?
ህወሓትን በማስወገድ የትግራይ ህዝብን በማንበርከክ አብዮታዊ ዲሞክራሲን በሐይል መደምሰስ ነው። በትግራይ ክልል ህዝብ ድምፅ ስልጣን ላይ የወጣውን የህወሓት ድርጅት ከስልጣን ማውረድ ነው። በአጭሩ በክልሉ የአስተዳደር ለውጥ (Regime change) በማካሄድ የቀለም አብዮት የተለመደ ዓላማ ማሳካት ነው።

ይህን ዓላማ በምን ስትራተጂና ታክቲክ ሊፈፅሙ አቅደዋል?
ዋናው ስትራተጂ ሰላም የሰፈነበትና የተረጋጋው የትግራይ ክልልን ማንኛውም ግርግር በመፍጠር የፈደራል መንግስት ጣልቃ ለመግባት የሚያስችል የተመቻቸ ሁኔታ ለመፍጠር መንቀሳቀስ  ነው። ይህን ስትራተጂ ብዙ ታክቲኮችን በመፈፀም ለማጠናከር እንዲያስችሏቸው ስልቶቻቸውን ቀይሰዋል። ባንዳዎችን በማደራጀትና ትልቅ በጀት መድበው ትግራይ ባለው ነፃ እንቅስቃሴ ተጠቅመው በትግራይ የሚታዩ አስተዳደራዊ ችግሮች ለቅመው እንዲታረሙ ሳይሆን በህዝብና በክልሉ መንግስት መካከል ልዩነት ሰፍቶ ግርግር እንዲፈጠር ማመቻቸት ነው።

ሌላው ስትራተጂ በኢትዮጵያና በኤርትራ የድንበር አካባቢ ያለውን የመሬት ይገባኛል ጥያቄ አመላለስ ጉዳይ የትግራይ ህዝብን ስሜት በሚጎዳ መንገድ መፍታት ነው፡፡ በዚህም ህዝቡ በህወሓት ላይ ያለው አመኔታና ፍቅር እንዲሸረሸርና ብሎም ተቃውሞ ተነስቶ የራሱን መንግስት እንዲያፈርስና ስልጣን በተላላኪዎች እንዲገባና የክልሉ ህዝብ እስካሁን የከፈለውን መስዋእትነት ዋጋ የሌለው አድርጎ ለማንበርከክ ምቹ ሁኔታ መፍጠር ነው።

በኤርትራ መንግስትና በኢትዮጵያ መንግስት መካከል ለህዝብ ግልፅና ይፋ ያልሆነው የሰላም ስምምነት መፈረሙ ይታወቃል። ይህን ስምምነት በመጠቀም በሁለቱ ህዝብ መካከል የናፍቆት ግንኙነት ተፈጥሮ ቆይቷል። የትግራይ ክልላዊ መንግስትም ሁለቱ ህዝቦች ያለምንም ዕንቅፋት እንዲገናኙ ከልብ በመነጨ ህዝባዊነትና የሰላም ፍላጎት በግልፅ በአደባባይ አውጆ በተግባርም ተንቀሳቅሷል። በዚህም በሁለቱ ህዝቦች መካከል በማንኛውም የትግራይ አካባቢ እንደፈለጉት እንዲንቀሳቀሱ አስችሏል። የአቶ ኢሳያስ አፈወርቅ መንግስት ይህን በሁለቱ አገሮች ህዝብ መካከል የተጀመረው ግንኙነት በቅን ልቦና ባለማየታቸው ማደናቀፍ ጀመሩ። የዛላንበሳንና ሰነዓፌን መሰመር ዘጉ። ራማ ዓድኻላን መስመር ዘጉ። ህዝቦች ሲደሰቱ አይወዱም እንዴ እስኪባሉ ድረስ ያለ መግለጫ ዘጋጉት። አንደገና የሁመራ ተሰኔ መስመር ከፈቱ ተብሎ ሁለቱ መሪዎች ህዝቡን እንደገና አስጨፈሩ። ተዘግተው የነበሩትም እንደገና ተከፈቱ። በሁለቱም መሪዎች እስካሁን ለመክፈት ካልተፈለገው የባድመ ባረንቱ መስመር ውጭ ሁሉም ተከፍቶ እንቅስቃሴ ተጀመረ። ተፈጥሮ የነበረው ስጋትና ተስፋ መቁረጥ እንደገና ታድሶ ነበር።

ብዙ ሳይቆይ ደግሞ የማይገመቱት ኢሳያስ አፈወርቅ በድንገት ሁሉንም ዘጋግተው ጭራሽ ሰራዊታቸውን በማዘጋጀት የውግያ ልምምድ ውስጥ ገቡ። ምሽግ ማስተካከልና ከምሽግ ውጭ ሊያጠቃ የሚችል ሐይል ማደራጀት ተያያዙት። ሰራዊት ሰብሰባ ላይ ሰላም ስምምነት ተደርጎ እያለ እንዴት ለጦርነት ተዘጋጁ ትሉናላቹ? ብሎ ተቃውሞ ሲያሰማ፣ ወታደር ናቹሁ የተባላቹሁትን መፈፀም ነው፡፡ እንዴት መሬታችን አሁንም በወያኔ ቁጥጥር ስር ሆኖ ለምን እንዘጋጀለን እንዴት ትላላቹህ ብለው መልሰው የወቀሱበት ሁኔታ ላይ እንገኛለን።

በትግራይ ላይ የቀለም አብዮቱ እንዲካሄድ ተስማምተዋል፡፡ ይህንን ስትራተጂ ለመተግበር የኤርትራ መንግስት ከአብይ መንግስት በመሆን በህወሓትና በትግራይ ህዝብ ላይ ጦርነት ለመክፈት እየሸረቡ ነው። ይህ ደግሞ የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት በማዳከምና በቀጭን ትዕዛዝ ምሽግ ልቀቁ ተብለው የኤርትራ መንግስት ጦር በቀላሉ ምሽጉን አልፈው እንዲገቡ ሊያደርግ ይችላል። ይህ ግምት ራሳቸው ኢሳያስ አፈወርቅ ካሉት የሚነሳ ነው፡፡ እንደሳቸው አባባል ከፌደራል መንግስት ችግር የለም ችግር ያለው ከወያኔ ነው ብለው ደጋግመው የገለፁት ጉዳይ በማየት ግምቱ ሚዛኑን ከፍ ያደርገዋል። ይህን በመፈፀም ትግራይን ማዳከምና ህዝቡን በመከፋፈል ህወሓትን ለአንዴና ለመጨረሻ መምታትና ፍላጎታቸውን በመደመር ቀለም አብዮት መፈፀም ነው።

ሌላው ሶስተኛው ስትራተጂ ሚድያን በመጠቀም መርዝ መርጨት ነው። ሚድያ አስተባብሮና እስካሁን የፈፀሙትን ዘመቻ አጠናክረውና በአዲስ ቅኝት ዘረኛና አደገኛ ፀረ ህዝብ ጥቁር ፕሮፖጋንዳቸውን በመሸፋፈን የትግራይ ህዝብ አዛኝ መስለው ባንዳዎችን እየተጠቀሙ በተከፈላቸው መጠን ይተጋሉ። መደበኛውንና ሶሻል ሚድያውን ውጤታማ ለማድረግ የውጭ ሃይሎችንም ቴክኖሎጂ ተጠቅመው ይንቀሳቀሳሉ። በውሸት ተመስርተው የሐሰት ዜና ደጋግመው በማቅረብ በህዝቡ የተወደዱ መሪዎቹ ላይ ጥላሸት በመቀባት ይደሰኩራሉ። በድህረ ገፆች ስም ያጠፋሉ። በአጋጣሚ የሚከሰቱ ችግሮች አጉልተው በማስጮህ ለሰላምና ለመፍትሔ ሳይሆን እንደ ሌሎች የኢትዮጵያ ክልልች ትግራይም ሁከት ያላትና ግርግር የበዛባት በማድረግ የእንስሳዋ እኔ ከሞትኩኝ … ስትራተጂ ለመከተል ምንም ግድ የላቸውም። ካልተሳካ ማበላሸትም አንዱ ስትራተጂያዊ ዓላማቸው ነው።

ማጠቃለያ
የትግራይ ህዝብ ተዘጋጅቶ ይህን በሱ ስም እየተዘጋጀ ያለውን የቀለም አብዮት በተለመደው የትግል ቆራጥነቱ እንደሚያከሽፈው ሳይታለም የተፈታ ነው። ማሸነፍ የሚችለው ደግሞ ብቃት ያለው ዝግጅትና የጠላቶቹ መሰሪ ባህርያትና ዝርዝር ስትራተጂና ታክቲክን አውቆ በንቃት ሲታገል ነው። ይህ ደግሞ ያለ መሪ ድርጅት አመራር የሚሳካ ትግል የለም።

የመደመር ቀለም አብዮት ካልተቀለበሰ የመጨረሻው ጦስ አገር መበተን ነው። በሊብያ፣ በየመንና በሶርያ ያየነው የቀለም አብዮት ውጤት በአገራችን ኢትዮጵያ እንዲደርስ መፍቀድ ነው፡፡ ስለዚህ አሁን እየተሸረበ ያለውን ሴራ በግልፅ ውይይት በማድረግና ህዝቡን በማስተባበርና በግዜ የለም መንፈስ ማዘጋጀትና የኢትዮጵያ ህዝቦችን በጎኑ አሰልፎ በመመከት ህወሓት እንደሁሌም በብቃት ሊመራ ይገባዋል። እንደገና እንደ ባለፉት ሦስት ዓመታት በቸልነት ወይም በብልጣብልጦች መታለል የለበትም። NEVER AGAIN ብሎ መነሳት አለበት። ህወሓት።

ሰማእታት ለዘላዓለም ክቡር ናቸው!