Sunday 12 January 2020

ኦህዴድ ከየት ወዴት? (ክፍል ሁለት)

ኡስማን ሙሉዓለም

በክፍል አንድ ፅሁፌ
ኦህዴድ እንዴት ከማጡ ወደ ድጡ እንደተንደረደረ ለማየት ሞክሬ ነበር፡፡ በክፍል ሁለት ላይ ኦህዴድ ግብዓተ መሬቱ እንዴት እንደተፋጠነ እናያለን፡፡

በኢትዮጵያ ህገመንግስት ይሁን በኢህአዴግ አሰራር ከኢህአዴግ ግንባር ድርጅቶች ማንም ሰው መመዘኛው ካሟላ የኢህአዴግ ሊቀመንበር ለመሆንና ብሎም ጠቅላይ ሚኒስተር ለመሆን የሚያግደው ነገር አልነበረም። ኦህዴድ አዲሱ ሊቀመንበሩን የኢህአዴግ ሊቀመንበር አድርጎ ካስመረጠ በኃላና ጠቅላይ ሚኒስትርነቱም ከተቆጣጠረ በኃላ በሁሉም የኦሮሞ ሊሂቃን ሊባል በሚችል ደረጃ አዲስ ክስተት እንደተፈጠረ ተደርጎ ነበር የተቆጠረው ወይም የተሰበከው።  ይህንን ሁኔታ ይቻል እንዳልነበረ ሆን ተብሎ ተሸፋፍኖ ለመጀመርያ ጊዜ ኦሮሞ ጠቅላይ ሚኒስተር ሆነ ተብሎ ተጋኖ ቀረበ። ትግራዋይም ወላይታም ለመጀመርያ ጊዜ ነበርኮ ጠቅላይ ሚኒስተር የሆኑት! ምን አሁን የተለየ ነገር ተፈጠረ የሚያስብልና የሚያስተዛዝብ ሆነ።

ይህ አሁን በአገሪትዋ ላይ የተፈጠረው ለውጥ/ነውጥ የቀየሱት ሰዎች ይህ የኢህአዴግ እምነትና አሰራር አጥንተውና አስጠንተው ባህርማዶ ላይ ሆነው አቅደውና ዝግጅት አድርገው ስለመሩት ነበር የተሳካ የቀለም አብዮት ያደረጉት፡፡ ይህ ቀለም የሌለው የቀለም አብዮት የተሳካው የኢህአዴግ አሰራር ዕድል ስለሰጣቸው ነበር። ይህም አድርገው ይኸው አሁን ወዳለንበት ትርምስምስ ያለ ሁኔታ ከተቱን። በኢትዮጵያ የነበረውን ፈጣን ዕድገት፣ ልማትና ዲሞክራሲ እንዳልነበረ ሰበኩ፡፡ የነበሩት ጉድለቶቹን ነቅሰውና አጉልተው በማውጣት የችግሩ ምንጭ አምታትተው ምክንያት ያልሆነውን ምክንያት አስደርገው ፈጣን ዕድገት ያስመጡልንን አብዮታዊ ዲሞክራሲያችን፣ ህገ መንግስታችንና ፌደራላዊ ስርዓታችንን ወነጀሉ፡፡ የህዝቡን ጥያቄዎች የማይመልስ መፍትሔ ብለው የስርዓት ለውጥ ብለው ወደ ባሰ ችግርና ትርምስ እንድንገባ ሆነ።

በስመ ኦሮሞ ስልጣን የያዙት ጠቅላይ ሚኒስተር መጀመርያ ላይ ኦህዴድና ምክትላቸው የነበሩትን ለማ መገርሳ፣ እነ አባዱላና ግርማ ብሩ ሳይቀሩ በሁሉም ጉዳይ ያማኩርዋቸው ነበር። ይህ ሲያደርጉ አብዮታዊ ዲሞክራሲን አጥብቀው የሚያምኑትንና ‘የህወሓት ተላላኪ’ አደረጉን የሚሉዋቸውን የድርጅቱ አበላት ስም ዝርዝር ይዘው በተለያየ ምክንያቶች ከአገር ውጭ ርቀው እንዲሄዱ አደረጉ፡፡ አበላቱ በየስብሰባው የለመዱትን በእኩልነት አስተያየት መስጠትና ሁሉም ውሳኔዎች በድምፅ እንዲወሰኑ የማድርግ ልምድ አዲሱ ሊቀመንበር አይፈልጉምና ለትምህርት፣ ለአምባሳደርነት እና ለተለያዩ ስራዎች እያሉ ከድርጅቱ ከኦህዴድ እንዲሩቁ አደረጉ። በመጨረሻም ለሳቸው የሚመቹትን ብቻ አሰባስበው የገደል ማሚቶ ስራ አስፈፃሚ ፈጠሩ።

ለማ መገርሳ ግን የለማ ቲም ያመጣው ለውጥ በሚባልበት ሁኔታ በቀላሉ የገደል ማሚቶ መሆን አልቻሉም። ጠቅላዩ መጀመርያ ስልጣን የያዙ ሰሞን ለማን አንተማ አለቃዬ ነህ! ብለው ቤተመንግስት ውስጥ አብረህኝ መኖር አለብህ ተቀራርበን እየተማከርን መስራት አለብን ብለው መኝታ ክፍል ተዘጋጅቶላቸው (ማን ያውቃል ሌላም ነገር ተዘጋጅቶላቸው ይሆናል) አብረው ተዳብለው መኖር ጀምረው ነበር። እንደዛ አብረህ እየኖርክ በየአደባባዩ በግልፅ የሚያሞግስህን ሰው ጠንከር ያለ ሃሳብ ማቅረብ ወይም ተቃውሞ ማቅረብ በጣም የመርሆ ሰው ካልሆንክ ይከብዳል። ለማ መገርሳም የከበዳቸውም ይመስለኛል። ለማ መገርሳ ግን አብይ ስመከረው እሺ ይልና ሌላ ነገር ይስራል፤ ከተነሳንበትና መነሻ ካደረግነው ዓላማ አፈንግጦ እየሄደ ነው ብለው ማማት የጀመሩት ብዙም ሳይቆዩ ነበር። ይህ በብዙ የኦሮሞ ሊሂቃን የሚታወቅ ጉዳይ ነበር። ለማ መገርሳ የስራ ምክንያት እያደረጉ ከቤተመንግስቱ መራቅና ከዛም ከሰውየው ጭራሽ የማይገናኙበት ሁኔታ እየተፈጠረ ሄደ። ተጣሉ የሚል ወሬ ሲበዛ አብይ የሆነ መድረክ ፈጥረው ወይም ለማ ያዘጋጀው መድረክ ካለ በድንገት ተገኝተው አንድ ላይ ነን ሞት ብቻ ነው የሚለየን ብለው ይመፃደቁና ህዝቡ፣ ሊሂቁ፣ ወዳጅም ጠላትም ያሳስታሉ። ድሮስ ሊያስመስሉ ብለው ነው እንጂ በመሃላቸው ንፋስም አይገባ ወይም ፀረ-ለውጥ ኃይሎች ሆን ብለው ያስወሩት ነበር አሰኝተው ጊዜ ይገዛሉ። ሰውዬው ኦህዴድን በዚህ ሁኔታ አስታግሰው ብአዴንና ግንቦት ሰባትን የሚያስደስት ነገር በፓርላማ ወይም በሆነ መድረክ ጣል ያደርጋሉ፡፡ እሳቸው ኦሮሞ ሳይሆኑ ንፁህ ኢትዮጵያዊ ናቸው ተብለው ግልብ ሁሉን ወደ ፈለጉበት አቅጣጫ ያስጋልብዋቸዋል።

በሌላ በኩል ደግሞ ከሰሜን ህወሓት ከደቡብ ኦነግ ሲቃወሙ የተለያዩ አልባልታዊ ምክንቶች ይደረድራሉ፡፡ ለሰሜኑ ተቃውሞ መያዣ የያዙዋቸውን ትግርኛ ተናጋሪዎችና የፖለቲካ እስረኞችን ልፈታ እያሰብኩ ነው እናንተ ተቃውሞቹሁን ለምን ለዘብ አታደርጉትም። ብአዴኖች እነ ደመቀና ገዱ ስለናንተ ብዙ ነገር እያነሱ እርምጃ ውሰድ እያሉኝ እኔ ሁኔታውን ለማብረድ እየጣርኩ ነኝ። እናንተም እያገዛችሁኝ አይደለም ብለው ለማለሳለስ ይሞክራል። የውጭ አማካሪዎች መቼ ምን ማድረግ እንዳለባቸው በቅድመ ተከተል አዘጋጅተው ይሰጥዋቸዋል። ነገር ግን አንዳንዴ ሰውዬው ጭብጨባ ሲበዛ ከተመከሩት ወጣ እያሉ እየዘላበዱ ያስቸግሯቸዋል። ነገር ግን ነገርየው ጊዜ ለመግዛት እንደሆነ ሁሉም ያውቀዋል፡፡ ኦነግን ደግሞ ከአስመራና ከካይሮ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ አምጥቻቹሁ ለምን ፋታ አትስጡኝም? ብለው መልእክት ይልኩባቸዋል። ሌላ ጊዜ አባገዳዎች ጠርተው ስልጣን ለመጀመርያ ጊዜ እኔ ኦሮሞ ልጃቹሁ ይዠ እንደማገዝ ኦነግ እየረበሹኝ ነው። ኦሮሞ መምራት እንደማይችል መልእክት እየተላለፈ ነው። አንዴ ይህ እጃችን የገባው ስልጣን ካጣነው መቼም መልሰን አናገኘውም። አሁን ኦሮሞዎች መተባበር ነው ያለብን በመካከላችን ሽኩቻ አያስፈልግም። ግድ የላቹሁም ጊዜ ለመግዛት አበሾችን አንደየሁኔታው አያያዝ ማድረግ አለብኝ። እነሱ ኦነግን ለምን ልኩ አታስገባውም? የህግ የበላይነት እያስከበርክ አይደለህም። ወደ ኦሮሞነትህ እያደላህ ነው እያሉኝ ነው። ሰለዚህ ኦነግን መክራችሁ ጭጭ አሰኙልኝ ብለው አባገዳዎችን ይልኩዋቸዋል። የእስስት ተለዋዋጭ ታክቲክ እና ስትራተጂ ተከትለው የስልጣን ዕድሜቸውን ለማራዘም ይጥራሉ።


አብይ አህመድ በተፈጥራቸው እሳቸው ተናግረው በጭብጨባ እንዲቀበልዋቸው ወይም ተሰብሳቢዎቹ እንዲሰሙ ብቻ እንጂ ጥያቄ አይወዱም። ከሁሉ በላይ ደግሞ ከኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ ውጭ ስብሰባ አይፈልጉም። እንኳን የኢህአዴግ ምክርቤት 180 ሰዎች ሰብስበው ስንቱ ጥያቄ አለኝ፣ ተቃውሞ አለኝና የተለየ ሃሳብ አለኝ ብሎ የሚነዘንዝ ካድሬ ያለበት ይቅርና የኦህዴድ ማእከላዊ ኮሚቴንም ሰብስበው አያቁም። የኢህአዴግ ምክር ቤት የሚፈሩት ጥያቄውንም ክርክሩንም ነበር። በመቶ ሰማንያ ሰው ፊት ተቃውሞ ቀረበ ማለት ለሳቸው ውርደት ነው። በተለይ ህወሓትና ከድርጅታቸው ነበር ኦህዴድ ለማ መገርሳ እየተቀባበሉ የአብይ አስተዳደር ግድፈትና ውድቀት እንዲነገር ጭራሽ አይፈልጉም። የኦህዴድ ማእከላዊ ኮሚቴን ስብሰባ የማይፈልጉት ግን ሌላ ምክንያት ነበራቸው። ነበር ሆኖ ቀረ አይደል።

አምባገነን አብይ ምን ይሳነዋል! ኦህዴድን ቀድሞ በግሉ አፈረሳት። ምክትላቸው የነበረው ለማ የኦህዴድ ማእከላዊ ኮሜቴ ስብሰባ እናድርግ ሲል ደንገጥ ብለው ለምን? ይላሉ። ህፃን ልጆች ሁነን አያ ጅቦ መጣ ስንባል እንደምንደነግጠው የማ/ኮሜቴ ስብሰባ ለአብይ የሚያስበረግግ ነበር። ለማ መገርሳና አብይ ይህን ማ/ኮሚቴ ይዘው ነበር በድንገተኝነት ምንም ግምገማ ሳይደረግ ሙክታርና አስቴርን አውርደው ለማና ወርቅነህ ገበየሁ (አሁን መጣያ አጥተው ካንዱ ወደ አንዱ እያንገላቱት ያለውን ሲፈጠር የጀርባ አጥንት ያልታደለውን) ሊቀመንበርና ምክትል ሊቀመንበር ያደረጉት። ታድያ ይህን የኦህዴድ ማ/ኮሚቴ መድረክ ፈርተው እንዳይደረግ ማድረጋቸው ስልጣንን ከሁሉም ነገር አብልጠው ለሚወዱ አብይ አህመድ እንደ ዋነኛ አደጋ ማየታቸው ምኑ ላይ ስህተት ሁኖ ሊታያቸው ይችላል።

አብዛኛው ፓለቲካ ላይ ያለ ሰው አብይ አህመድ ቀድሞ ማጥፋት የሚፈልጉት ኢህአዴግን ይመስለዋል። በኔ ግምት ግን አብይ አህመድ ቀድሞ ማጥፋት የሚፈልጉት ብቻ ሳይሆን ቀድመው ያጠፉት ኦህዴድን ነው። ምርጥ የኦህዴድ አመራሮችና ካድሬዎችን በማጥፋት ከስልጣን በማውረድ ምርጥ የመሬት ቸብቻቢዎች ሌቦችን በአደባባይ የሚታወቁ ጉበኞች እንደ ብርሃኑ ፀጋዬ፣ ደምመላሽ ገብረሚካኤል፣ ሽመልስ፣ አዳነችና ሌሎችም ወደፊት አምጥተው ሾሙ። ምርጥ ካድሬዎችና ለኦሮሞ ህዝብ የሚታገሉትን ገድለውና አስገድለው የቀሩትንም ለውጥ ያስፈልጋል በሚል በምትካቸው ሌቦችንና ጉበኞች ህዝቡ የተማረረባቸው ቦታ እየቀያየሩ ሾሟቸው። የለውጥ መዝሙር በባዶ ቦታ ዘመሩ። የኦሮሞ ህዝብ በተለይም የወጣቶች (የቄሮዎች) ጥያቄዎች እንኳን ሊመልሱ የባሰ በለውጥ ሂደት ነው ያለነው ችግሩ በሽግግር ወቅት የሚፈጠር ነው። ቻሉት! ብለው ይመልሳሉ። ጥያቄው አፍጥቶ ሲመጣባቸው ደግሞ ሦስተኛ ወገን፣ ፀረ ለውጥ ኃይሎችና ኦሮሞ አገር ማስተዳደር እንደማይችል ለማሳየት የሚፈልጉ ወገኖች ችግር እየፈጠሩ ስለሆነ የናንተን ችግር ተረጋግተን አጥንተን መፍታት አሁን አንችልም ታገሱን ይላሉ።

አሁን በአገራችን ኦህዴድ የሚመራው ለውጥ አንዳንዴም ኦሮሞ የሚመራው መንግስት ቢባልም በተጨባጭ የአገሪቱ መሪዎቹ ግን ቅጥረኛው አብይና ቅጥረኞቹ አክራሪ ኒዮ ሊበራል ኃይሎች ናቸው። ከቄሮ ትግል ጀምሮ የነበረው ዋና ድብቅ ዓላማ ቅጥረኛውንና ጥገኛ ሃይል ስልጣን ላይ አውጥቶ ኢትዮጵያን ራሷን እንዳትችል በማድረግ በነሱ ትዕዛዝ የምትመራ ማድረግ ነው። የቄሮ የስራ ማጣት፣ የህዝቡ መልካም አስተዳደር እጦት ጥያቄ ጉዳያቸው አልነበረም። በጭቁኖች መካከል ህብረት እንዳይኖር አድርገው የቄሮ ትግል ውጤታማ እንዳይሆንና ወደ ፀረ-ህወሓት፣ ፀረ-የትግራይ ህዝብና ፀረ-ትግርኛ ተናጋሪ ፊታቸውን እንዲያዞሩ ያደረገው በኦህዴድ የበቀለው አረም አመራር የፈጠረው ለውጥ አይደለም። ይህ እንደሚመጣ ህወሓቶች በምርጫው ምሽት አጥብቀው ተቃወሙ። እነ በረከት ስምኦን ከብአዴን እነ ስራጅ ፈርጌሳ ከደህዴን ተቃወሙ። በረከት ስምኦን ለእስር የዳረገውን ትንቢት የሚመስል የተቃውሞ ንግግር ያደረገውም ያኔ ነበር። በረከት አብይ ከተመረጠ አገራችንን አሳልፈን ለውጭ ሃይሎች የምንሰጥበት ሁኔታ እንደሚፈጠር በማስረጃ አቀረበ። እነ አዳነችና ለማ መገርሳም አብይ እደዛ እንዳልሆነ በማስረጃ ሳይሆን ባዶ ቃላቶችን ተጠቅመው ሰበካ የሚመስል ንግግር አድርገው በውጭ አብዛኛውን የምክርቤት አባል መልምለውና ገዝተው ያስገቡትን እንዳይፈርሱባቸው ተከራከሩ። ቤቱ ትክክለኛውን አደጋ እንዳያይ አደረጉት፡፡ አብይ ተመረጠ። አለቀ። ለኔ በአጠቃላይ የለውጡ ትግሉ የተቀለበሰው እነ አብይ ስልጣን ሲይዙ ያኔ ነበር።
ኦህዴድ ታድሶ እነ ለማንና አብይን ወርቅነህን ጠራርጎ ቢታደስ ኖሮ ለውጡ አይቀለበስም ነበር። ኦህዴድ የኦሮሞን ህዝብ ጥያቄ የከዳው ፎርማሊ በዚች ቀን ነበር። ፎርማሊ ያልኩት ኦህዴድ ዝቅጠቱ የቆየ ቢሆንም በጥልቀት ተሃድሶ ይታደስ ይሆናል የሚል ግምት ስለነበር ነው። ኦህዴድ መቼም የማያስቆጭ ፕሮግራም ሽጦ ኦሮማራ ብሎ እንደሱ ከዘቀጡት የብአዴን አባላት ጋር አበረ፡፡ ከጎሹ ወልዴና ካሳ ከበደ የሚሞዳመድ ሆነ፡፡ አዲሶቹ ደርጎች በወጣትነት ዕድሜያቸው አሮጌ ብትቶ አስተሳሰብ አንጎላቸው ከሞላው ጋር ግንባር ፈጥረው ሲንቀሳቀሱ ነበር የኔ ለውጡ የተቀለበሰው። ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው፣ ስንኖር ኢትዮጵያውያን ስንሞት ኢትዮጵያውያን ሲባል ያኔ ነበር ለውጡ የተቀለበሰው። የቄሮ ትግል የከሸፈው! ለዘለቄታው የማይጠፋ ቢሆንም ትግሉ ውጤታማ ሳይሆን የቀረው። በተመሳሳይም የአማራ ህዝብም ትግል የለውጥ ፍላጎት የከሸፈው በዚሁ ደቂቃና ሰዓት ነበር።

ያልታደሰ ኢህአዴግ ለውጥ ሊያመጣ አይችልም። ለዚህ ነው አብይን የወለደ የዘቀጠ ኢህአዴግ ወርቅ የሆነ ፕሮራም ይዞ የሞተው። አርማጌዶን እንዲሁ ቅርብ የሚገኝ ሳይመስለን ራሳችንን አርማጌዶን ውስጥ አገኘንው። ኢህአዴግ ተልእኮውን ሳይፈፅም በውስጡ በበሰበሱ ትሎች ተበልቶ የተጋደመው። የፈጠሩት ድርጅቶችም ከዚህ ውጭ አልሆኑም፡፡ ደህዴን ከላይ የነበረ ቢመስልም የኦህዴድ ተላላኪ መሆን ፀጋ ነበር እያለ የአብይ አህመድ ተላላኪ ሆነ፡፡ በጣት የሚቆጦሩ መሪዎች ደህዴን የሚለውን ስም ይዞ ተበታተነ። ሃይለማርያም በታሪክ የሚወሳበት ታሪክ ካላ የብተና ታሪክ ነው። ኦህዴድ የተጠጋው ብአዴንም በውስጥ ሽኩቻ ለራሱም ለደባሉ ኦህዴድም ሳይሆን ቀርቶ ከአብን ልወዳደር ብሎ ምኑም ሳይችለው ውስጡ ታመሰ። የተረከባትን ክልል አንድና ሰላም ያላት አድርጎ መምራት ተሳነው። እርስበርስ እየተፎካከሩ የቲም ለማ የቁርጥ ቀን አባል ተብለው የሚታወቁት ገዱ ክልሉ ውስጥ በሰላም መኖር ሳይችሉ ቀርተው ለህይወታቸው ሰግተው አዲስ አበባ ቦሌ አካባቢ በሚገኘው የጀግናው ቀነኒሳ ሆቴል ውስጥ ከሁለት ሳምንት በላይ መሽገው ቆዩ (በነገራችን ላይ በኮፒራይት ህግ ሳይጠየቁ አይቀሩም መቐለ አክሱም ሆቴል ላይ እንደ መሸጉት በመመሸጋቸው)። ገዱም የሃይለማርያም ደሳለኝ ዓይነት ሁኔታ ገጠማቸው፡፡ በሽምግልና በፈቃዳቸው ስልጣን እለቃለሁ አሉ ተብለው ነብሳቸው ይማርና ለአምባቸው ስልጣኑንም አደጋውንም ጭምር አስረክበው ውጭ ጉዳይ ሚኒስተር ተባሉ። እንደተፈራውም አምባቸው በገዛ ቢሮቸው በጭካኔ በጥይት ተደብድበው ተገደሉ። ኦህዴድ በማይመራው መንግስት ኦሮሞ በማያስተዳድረው ስርዓት እንዴት ተጠያቂ ማድረግ ይቻላል? ኦህዴድ የአብይ አህመድ የፈረስ ስማቸው እንደሆነ እንጂ የትኛው ክልል ነው ያስተዳደረው፡፡ ኢትዮጵያን ይቅርና ኦሮሚያንም ማስተዳደር አቅቶት አይደለም እንዴ ለጄነራል ብርሀኑ ጁላ በወታደራዊ ኮማንድ ፖስት እንዲያስተዳደሩለት ያስረከበው፡፡ ክልሉ በአጭሩ የጦርነት ቀጠና ሁኗል፡፡ አብይ አህመድ ከሚንሰፈሰፍላቸው ያለፉት ጨቃኝ ሰርዓቶች ፊፃሜ አልተማረም፡፡ ጨካኙ አፄ ኃይለሥላሴ የእንግሊዝ አውሮፕላን ተበድረው በመቐለ እና ጨካኙ ደርግ በሐውዜን ህዝብ በተሰበሰበበት የገበያ ቀን የሚያስተዳድሩት ህዝብ እንደጨፈጨፉት የሚታወስ ነው፡፡ አብይ አህመድ በአጭሩ የስልጣን ዕድሜ ዘመኑ የወለጋ ህዝብ ተቃውሞን ለመጨፍለቅ በቀርቡ ጊዜ ሁለቴ በሄሊኮፕተር ከሰማይ እሳት የጎረሰ የፋክራስ ቦንብ አርከፈክፎባቸዋል። አብይ መስሎት እንጂ በአውሮፕላን ድብደባ የተገታ ትግል የትም አገር አልታየም።

ኦህዴድ ወደ ጭንቅላቱ ጫፍ ላይ በስብሶ ገምቶ ቢሆንም የፓርቲ ውስጥ ትግል/ አብዮት ቢደረግ የመዳን ዕድል አልነበረውም ማለት አይቻልም። ከላይኛው ካድሬ ጥቂቶች ከመካከለኛው ደግሞ ቀላል ያልሆኑትና ከታችኛው ደግሞ አብዛኛው ጨርሶ ህዝባዊነቱን ያላጠፋና መስመሩን ያልከዳ ቢያንስ ደግሞ ኦሮሞ ብሄርተኝነቱን ያልሸጠ ስለነበረ እስከቅርብ ግዜ ድረስ ተስፋ ሲደርግበት ነበር። የዚህ ማስረጃ በእንደመር ውይይት ወቅት ያነሳቸው የነበሩት ጥያቄዎች ማስረጃ ናቸው። የለማ መገርሳ የረፈደበት የቁጭት አቋም ይዞ ጠይቋል። ተከራክሯል። ፀረ ዲሞክራሲ የሆነው አብይ አህመድና ቡዱኑ የካድሬዎቹ ተቃውሞ ረጋግጠው እና አስፈራርተው አለፉት እንጂ። ምክትል ሊቀመንበሩ ያልተገኘበት፣ ሳይታወጅና በምን አሰራር እንደተጠራ የማይታወቀው የኦህዴድ ጉባኤ ተብዬ መድረክም ቢሆንም አልጋባልጋ ሆኖ መደመሩንና መበልጠጉን አልተቀበለም። በድምፅ ሳይሆን ሙሉ በሙሉ ተቀበሉት ብለው ራሳቸው ሊቀመንበሩ ከጉባኤው በላይ ሆነው በስሙ አወጁ።

ኦህዴድ የግል ካምፓኒያቸው ይመስል ከስሟል ብለው አከሰሙት። የኦህዴድን ቢሮዎች ለብልጥግናቸው አስተላለፉዋቸው። ለማ መገርሳ ኦህዴድን ይዘው ከሌሎች የኦሮሞ ድርጅቶች የፈጠሩት ጥላ ውስጥ የነበረው ኦህዴድ ከጥላው ስር ወጥቶ ጠፋባቸው። ምን ቀራቸው? ምንም! በነገራችን ላይ ኦነግ በጣም ብዙ የትግል አካሄዱ ውስጥ የተንፀባረቁ ትላልቅና መሰረታዊ ስህተቶች ቢኖሩትም (እዚህ መዘርዘሩ ከአጀንዳዬ ያስወጣኛል) መቼም ቢሆን ለደቂቃም የኦሮሞ ህዝብ ራስን በራስ የማስተዳደር እድልን ከድቶም ሽጦም አያውቅም። ኦህዴድ ይዞት የነበረውን ይህን ክቡር ህዝባዊ ዓላማ ክዶ አማሟቱ ሳይታወቅ እንደ ፀጉራም ውሻ አለሁ እያለ ላይመለስ አሸለበ። የከፈለው ከባድ መስዋዕትነት ተረሳ። ድርጅቱን ለስልጣን ብለው አገር ለሚሸጡ የፖለቲካ ነጋዴዎች አሳልፎ ሰጠ።

የኦህዴድ ዲቃላ ልጅ አፋን ኦሮሞ በመቻሉ ብቻ ለኦሮሞ ይቆማል ብሎ መገመት ስህተት ነው። ይህ ብዙ ጊዜ በሁሉም ትግሎች ታሪክ የተከሰተና የታየ ስህተት ነው። ባንዳዎች በሁሉም የትግል እንቅስቃሴዎች ለስልጣን፣ ለገንዘብ እና ለሌላ ጥቅሞች ለማግኘት ብለው አገራቸውን ህዝባቸውን ቤተሰባቸውንም ጭምር ይሸጣሉ። ከኦህዴድ ወደ ባንዳው ብልጥግና የተካሄዶው ሽግግር የቀለም አብዮት ውጤት ነው። የቀለም አብዮቶኞች የሚያማምሩ ቃላቶችን በመደርደር ቀለም በማንፀባረቅ የህዝብን ቀልብ በመስረቅ፣ በማፍዘዝና በማደንዘዝ እርካብና መንበርን ይዞ ዕድሜ ለማስረዘም ይሞክራሉ። አብይ አህመድ ከኦህዴድ ውጭ በግልፅ ኦሮማራ አደራጁ። በድብቅ ከሃይማኖታቸው የተሳሰረ ማይንድ ሴት የሚባል ፎረም በምህረት ደበበ በተባለ የስነልቦና ሃኪማቸው የሚመራ ድርጅት አላቸው። ሁለቴ ብቻ በግልፅ ሲሰበሰቡ አይተናል። ስልጣን ከመያዛቸው በፊትና ከያዙ በኃላም የምስጋና መድረክ ተዘጋጅቶ ተገኝተዋል። ከዚህ ውጭ አሜሪካ አገር እየሄዱ ከጁሓርና ከግንቦት ሰባት የፈጠሩት ጥምረትም ሌሎች ለስልጣን ሲሉ የተጠቀሙባቸው ድርጅቶቻቸው ናቸው። ከውጭ መንግስታት የተፈራረሙትን የቅጥር ስራቸውም ሌላው ለስልጣን ያበቃቸውና አሁንም በስልጣን እንዲቆዩ እያደረጋቸው ያለ አቅም ነው። ለዚህም ማሳያ ምንም ለውጥ ያላመጣና የአገር ሉዓላዊነትን አሳልፎ የሰጠ ሰው የኖቤል ተሸላሚ ማድረግ በላይ ማረጋገጫ የለም። ይህም አለም ያወቀወ ፀሀይ የሞቆው እውነታ ነው፡፡  


አብይ አህመድ ኦህዴድና አገራችን ለበለፀጉ አገሮች ሽጦ ስለበለፀገ ብልጥግና ፓርቲ ስትሞላቀቅ ደግሞ ፒፒ የምትባል ፓርቲ ፈጠረ። ለውሻ ደስ የሚል ስም ነው ብዬ ውሻዬን ፒፒ ብዬ ስም አወጣሁላት። የሚከለክል ህግ ያለ አይመስለኝም። ህግ በፈረሰበት አገር ደግሞ ስለ ህግ ምን አስጨነቀኝ።

ቸር እንሰንብት እንላቹሀለን እኔና ፒፒ ውሻዬ በጋራ!

(ምንጭ : አይጋ ፎረም )




No comments: