Monday 8 October 2018

የሶስት ፈራጆች ወግ:_ ዋለልኝ መኮንን፣ ትህነግ/ህወሓት እና ግንቦት 7 – (ጌታቸው ሺፈራው)

Image may contain: text
ዋለልኝ መኮንን በተማሪዎቹ ንቅናቄ ወቅት ስሙ የተጠራ ሰው። ትውልዱ ከወሎ የሆነው ዋለልኝ አብዛኛው ውሎው በኋላ ሻዕቢያ እና ትህነግን ከመሰረቱት አማራ ጠል፣ የተገንጣይ ቡድን መሰረቶች ጋር ሲሆን ህይወቱ ያለፈውም ከእሱ ጋር የጠበቀ ግንኙነት እንደነበራት የሚነገርላት እና የተገንጣዮቹ ህዋስ ከሆነችው ማርታ መብትሃቱ ጋር አውሮፕላን ሊጠልፍ ሲሞክር እንደነበር ታሪክ ያስረዳል።
ዋለልኝ መኮንንን በወቅቱ ንቁ የተማሪው ንቅናቄ አባል የነበር ሲሆን አሁንም ድረስ በክፉም በደጉም ስሙን የሚያስጠራው ለተገንጣዮቹ የሰጠው “ርዕዮታለማዊ” መሳርያ ነው።
ዋለልኝ የብሄሮች ጥያቄ በሚል መጣጥፉ የአንደኛው ማህበረሰብ ነው የሚባልና ሌላኛው ወድዶ እና ፈልጎ የሚበላውን ዶሮ ወጥ ሳይቀር የተጫነ ነው ብሎ በመስበክ “አማራው ጨቋኝ ነው” ብሎ ቀስቅሷል። አነጋጋሪው ዋለልኝ በወቅቱ የሚበላውን፣ የሚለበሰውን “የአማራ እና የትግሬ” ብለው የገለፀው ቢሆንም ትህነግ እና ሻዕቢያን የመሰረቱት “የትግራይ” የሚለውን ፍረጃ አንስተው “የአማራ” የምትለዋን ብቻ ቀጠሉ።
No automatic alt text available.
ትህነግ/ህወሓት አማራውን ገዥ አድርጎ ባቀረበው ማንፌስቶው በብሔር ትርክት ላይ የወሰደው “የትግራይ” የሚለውን ቆርጦ፣ የዋለልኝን ትርክትም ጭምር ነው። ትህነግ/ህወሓት በዚህ ማንፌስቶው እነ አሉላ አባነጋ ጨምሮ ከወደትግራይ የጦሩ ቁንጮ የነበሩበትን፣ ፖለቲከኞቹን፣ ባላባቶችን በመተው ስርዓቱን የምኒልክ፣ አጤ ምኒልክ የሚመራውም ስርዓት የአማራ አድርገው በመፈረጅ ብዙ ቅስቀሳ አድርገውበታል። ከአጤ ዮሀንስ በፊት የነበሩትንም “የአማራ እና የትግሬ” በማለት፣ በተለይ አማራው የትግራይን ሕዝብ ለመበደል ሲል የትግራይ ገዥዎችን ሲያዳክም መኖሩን በሰነድ ሳይቀር አትተዋል።
ትህነግ/ህወሓት በግልፅ አይናገረው እንጅ የትግራይ ገዥዎችን የአማራ ብሔር ከስልጣን እየገፋ (እየተፈራረቁ) ሲገዙ መኖራቸውን በጥቅሉ ተቀምጧል። ይህ ግን ሲቀመጥ የአጤ ዮሃንስ መንግስት በውስጡ የትኛውንም ያካትት የትግራይ ተብሎ፣ በታሪክ በመልካምነቱ ሲወሳ፣ የሌሎቹ የአማራ ተብለው በክፉነታቸው ተቀስቅሶባቸዋል። እንደ ትህነግ/ህወሓት አማራው ሲመጣ መከራ፣ ትግሬው ሲተካው ድሎትና መልካም ነገር እየተከተለ ሲፈራረቁ እንደነበሩ ያትታል። በእርግጥ ትህነግ/ህወሓት እንደምናውቀው ባህሪው እና ለትግራይ ሕዝብ ቆሜያለሁ እስካለ ድረስ እስከ አመተ ፍዳም ወርዶ “የትግራይ ነበር፣ የአማራ ነበር፣ ትግራይን በደሏል” የሚለው አገዛዝ ቢኖር አይገርምም። ይህ የትህነግ/ህወሓት አማራ ሲመጣ በደል፣ ትግሬ ሲመጣ ድሎት እያለ በጥላቻ መነፀሩ “አማራ እና ትግሬ እየተፈራረቁ” የሚል ትርክቱ በዛሬው ዘመን፣ ያውም የኢትዮጵያ አንድነትን ለማቀንቀን ግንባር ቀደም ነኝ በሚል አካል መቀንቀኑ የዋለልኝ፣ የትህነግ/ህወሓት ትርክት አሁንም በዘመናዊ ፖለቲካ በአማራው ላይ እየጮኸ መሆኑን ያሳያል።
ግንቦት 7 የኢትዮጵያ አንድነትን በመስበክ ላይ ይገኛል። የዚህ ድርጅት ከ80 እስከ 90 በመቶው የሚሆኑት አባላት፣ በተለይም ታጋዮች ከእነ ዋለልኝ ጀምሮ፣ በትህነግ እና ሌሎች ተገንጣዮች ከተዘመተበት አማራው የተገኙ ናቸው። ሆኖም በእነዚህ ታጋዮች “መጣሁ ደረስኩ” ሲል የኖረው እና አሁንም ከአማራው ውጭ ለመንቀሳቀስ እጅ ተወርች የተያዘው ግንቦት 7 ከትህነግ/ህወሓት እና ዋለልኝ መኮንን ጋር በሚያመሳስለው የፖለቲካ ትርክት መቀጠሉን የፖለቲካ ሰነዶቹ እያረጋገጡ ነው። ግንቦት 7 የአሜሪካው ፕሬዝደንት ባራክ ኦባማ በተመረጠ ወቅት “ኦባማ ተመረጠ። አለም ተደሰተ።………” ብሎ ባወጣው መግለጫ “ሀገራችን ኢትዮጵያ ለአስርት መቶ አመታት እየተፈራረቀ ሲገዛ የኖረው የአማራ እና የትግሬ ልሂቃን የኢትዮጵያ ሕዝብ ፍላጎት እስከሆነ ድረስ ለደቡቡ፣ ለኦሮሞው፣ ለአኙዋኩ፣ ለመልቀቅ ፈቃደኛ የማይሆንበት ምክንያት የለም” ይላል። ይህ ርዕሰ አንቀፅ እነ ዋለልኝ መኮንን “አማራ እና ትግሬ እየተፈራረቁ” ካሉበት 50 አመት በኋላ የተደገመ ትርክት ነው፣ ይህ የግንቦት 7 “እየተፈራረቁ” ትርክት፣ ትህነግ/ህወሓት አማራ እና ትግሬ እየተፈራረቁ (አማራ ሲመጣ መከራ፣ ትግሬ ሲመጣ ድሎት) ብሎ በሰነድ ካሰፈረ አርባ አመት በኋላ የተደገመ ነው።
Image may contain: text
የዋለልኝ፣ በተለይም የትህነግ/ህወሓት አላማ ግልፅ ነው። ሕዝብን ጠላት ብሎ የፈረጀ ነው። በእርግጥ ትህነግ/ህወሓት ይህን የ”እየተፈራረቁ” የጥላቻ ትርክት ሲፅፍ ለትግራይ ወግኖ፣ አማራውም ፈርጆ ነው። በእርግጥ ዋለልኝ አማራ እና ትግሬ እየተፈራረቁ ሲል “የብሔር ጥያቄ” የሚል የወቅቱን የፖለቲካ ፋሽን እያወራ ስለነበር ነው። ከአርባ እና 50 አመት በኋላ ይህን የ”እየተፈራረቁ” ትርክት የደገመው ግንቦት 7 ስለ አሜሪካ ፕሬዝደንት መመረጥ ርዕሰ አንቀፅ በፃፈበት ወቅት ነው።
ግንቦት 7 ላነሳው የትህነግ/ህወሓት ትርክት በወቅቱ ፖለቲካ ያሉ፣ ምን አልባትም ለመሪዎቹ የሚቀርቡትን፣ ያውም በብሔር ማንነት የተደራጀ ፓርቲ መሪ የሆኑትን እነ ዶክተር መረራን ክርክር ማንሳት ይቻላል። እነ ዶክተር መረራ ተገንጣዮቹ የ”አማራ ስርዓቶች” የሚሏቸውን፣ ትህነግ፣ ዋለልኝ እና ግንቦት 7 “አማራ ኢትዮጵያን እየተፈራረቀ ሲገዛ ነበር” ለሚለው የጥላቻ ትርክት በተደጋጋሚ ክርክር ሲሰጡ ተሰምተዋል። ዶክተር መረራ ጉዲና ስርዓቱን ብቻ ሳይሆን እነ እያሱን፣ እነ ቀዳማዊ ኃይለስላሴን፣ ከዚህም ሲያልፍ እን አጤ ምኒልክን እንዲሁም ዋና ዋና ባለመዋሎቻቸውን “ኦሮሞዎች ናቸው” እያሉ በይፋ ተሟግተዋል። ከዛም አለፍ ሲል የየጁ ስርወመንግስት፣ እንዲሁም የጎንደር መኳንንትና ነገስታት ድረስ ምሳሌዎችን በማንሳት “ኦሮሞዎች አሉበት” በማለት ተሟግተዋል። የዶክተር መረራ ክርክሮች እውነታ ነው አይደለም የሚለው በተለያየ ጎራ ያለውን ሊያከራክር ይችላል። ዋናው ቁም ነገር ግን ግንቦት 7 የብሔር ፖለቲካን ከሚያራምዱት እነ ዶክተር መረራ “አገዛዞቹ የብዙዎች ነበሩ” ከሚሉት በተቃራኒ ከለዘብተኞቹ ብሔርተኞች ዘልሎ ከፅንፈኞቹና በጥላቻ ከናወዙት የትህነግ እና የሻቢያ ትርክት ማሳ ለማሳ መገኘቱ አስገራሚ ነው።
በእርግጥ በውስጣቸው ይይዙታል እንጅ ትህነግ/ህወሓትና ሌሎቹ ፅንፈኞችም በዚህ ዘመን “እየተፈራረቁ” የሚለውን የጥላቻ ቅስቀሳ አሁን አይጠቀሙበትም። ግንቦት 7ን እያወዳደርነው ያለነው ከ40 አመት በፊት ጥላቻቸውን ሲረጩ ከነበሩት እንዲሁም፣ በዛሬ ዘመንም ቢሆን “ተፈራረቁ የሚባሉት አማራና ትግሬ ብቻ አልነበሩም” ብለው በይፋ ከሚከራከሩት ብሔርተኞች ጋር ጭምር ነው። በዚህ ረገድ ግንቦት 7 በሻዕቢያ አቀነባበሪነት ተልዕኮ ለመፈፀም ሲጥር የተገደለውን ዋለልኝ፣ ስለ አማራ የፃፈውም ሰነድ “ተችዋለሁ፣ ስህተት ነው” ያለው ትህነግ/ህወሓት “እየተፈራተቁ” ፖለቲካ በቅርስነት እያስቀጠለ መሆን አለበት።
No automatic alt text available.
ከትርክቱ ጀርባ:_
1) “እየተፈራረቁ” ሲገዙ ኖረዋል የሚለው ቅስቀሳ ሀገር፣ የአንድ ወገን ፕሮጀክት እንጅ በየአደባባዩ እንደምንሰማው የሁሉም አይደለችም ከማለቱ ባሻገር፣ ሀገር ገንቢዎችን በመውቀስ ላይ ያተኮረው የተገንጣዮች ትርክት ቅሪት ነው
2) “ሲፈራረቁ” ኖረዋል የሚለው ቅስቀሳ የቀደሙትን ሀገር ገንቢዎች በመውቀስ፣ በመወንጀል ላይ ያተኮረ በመሆን ብቻ አያበቃም። ላለፉት ስርዓቶች ቀጣዩ መቀጣት፣ እዳ መክፈል አለበት። ለዚህም “ለደቡቡ፣ ለኦሮሞው፣ ለአኙዋኩ መልቀቅ አለባቸው” ብሎ በግልፅ አስፍሮታል። ይህ ማለት ባለፉት መቶ፣ ሁለት መቶ፣ ሶስት መቶ አመታት ስልጣን ላይ ነበሩ ብሎ ለፈረጃቸው፣ ቀጣዩ ትውልድ ሀሳቡ፣ አቅሙ፣ብቃቱ… ……ከምንም ሳይገባ ከፖለቲካው መገለል አለበት ማለት ነው።
3) ይህ ለዘብ ብሎ የቀረበ የሚመስል “ለኦሮሞው፣ ለደቡቡ…… ይልቀቅ” መግለጫን ከዘመኑ ፖለቲካ ጋር ስንመዝነው፣ ግንቦት 7 የአማራውን መደራጀት የሚፀየፈው “ኢትዮጵያ ትፈርሳለች” ከሚል ቀና ትንታኔ ነው ብሎ መገመት የዋህነት ይሆናል።

No automatic alt text available.
Image may contain: text

ከአክሱም ፖስት ተጨማሪ
 የብህረሰቦች ጥያቄ አሁንም በኢትዮጵያ መልስ አላገኘም :: "በሄረሰቦች" በማነነታቸው ከመሸማቀቅ ወያኔ አድናቸዋለች:: ለዚህም ምስጋና ለሕዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ (ህወሓት) ኢትዮጵያውያን ያቀርባሉ :: ይሁንና አሁንም የአማራ ሊህቃን ለኢትዮጵያዉን አኩልነትና አንድነት አንቅፋት ሆነዋል::አማርኛ ብቻ አገራዊ ቆአንቃ  መሆን የለበትም:: ትግርኛ: ኦሮምኛ: ሶማለኛና ሌሎችም ደረጃቸው አየታየ አገራዊ ቆንቆአ መሆን አለባቸው: የአገውና የቅማንት; የሲዳማ ሕዝብ ግዛትም ተወስኖ አንደ  ትግራይ;አማራና ኦሮሞ ጋምቤላ ሆነው አንደ  ከፈለ  ሀገር አንደደራጅ መደረግ አለበት :: ክልል የሚለው ስያሜም ወደ ክፍለ ሀገር በሚል አንዲተካ መደረግ አለበት:: የአማራ ሊሕቃን አሁንም ለኢትዮጵያ ሕዝብ አኩልነትና አንድነት አንዲቆሙ ይጠየቃሉ::

 

No comments: