Wednesday 10 October 2018

የራያ ጉዳይ የማንነት ወይስ የመልካም አስተዳደር ችግር?

በተለያዩ የዓለም ክፍሎች የሚንገኝ የራያ ተወላጆች እና ሙሁራን

1. መግቢያ
“ራያ” የሚለው ቃል አመጣጡ በግልፅ ባይታወቅም በአፈ-ታሪክ ደረጃ የተለያየ ትርጉም ይሰጠዋል። አንዳንዶቹ “ራያ” የሚለው ቃል የትግርኛ ቃል ሲሆን ከደጋው ራያ የሚኖሩ ሰዎች በክረምት ጊዜ ሜዳው ሲያዩት በጣም ጫካ፣ ለምለም እና እጅግ ደስ የሚል ስለነበረ “ረአያ” (በአማርኛ እያት) ሲሉ ቀስ በቀስ “ረአያ” ወደ “ራያ” ተለወጠ ይላሉ። ሌላ ከዚህ ጋር በተያያዘ በደጋው አከባቢ ላይ የነበሩ መሳፍንቶች ቦታው በጣም ለምለምና ምቹ ነው ሲባሉ ይቺን ቦታ መቼ ነው የሚናያት (መኣዚ የና “ንርእያ”) አሉ ይባላል። ከዛም “ንርእያ” የሚል ቃል በሂደት ወደ “ራያ” እንደተቀየረ ይነገራል። 

ሌሎቹ ደግሞ “ራያ” የሚለው ቃል የኦሮምኛ ቃል እንደሆነና ትርጉሙም “ሰራዊት” ማለት እንደሆነ ይገልፃሉ። ከዚህ በተያያዘ ኦሮሞች ግዛትን ለማስፋፋት በሚመጡበት ጊዜ ወጀራት በሚባለው አከባቢ በተካሄደው ጦርነት እንደተሸነፉና ሰራዊቱን እዛ ተበታትነው የቀሩ ሲሆን የሰራዊቱ ስም “ራያ” ይባል ስለነበረ ይህን ለማስታወስ “ራያ” እንደተባለ ይነገራል። በሌላ በኩል ደግሞ ወደ ራያ የመጡ የኦሮሞ ጎሳዎች “ራይቲ” ከሚትባል የሀረር ቦታ ስለመጡ ያቺ ቦታ ለማስታወስ ነው ይላሉ። “ራይቲ” የሚል ቃል በሂደት ወደ “ራያ” እንደተቀየረ በአፈ-ታሪክ ይነገራል።
በዚህ መሰረት ራያ ከሒዋነ (አንዳንዴም ከዓዲ ጉዶም ወዲህ ይላሉ) እስከ አልውሃ ድረስ ያለውን ቦታ የሚያጠቃልል እንደሆነ ትላልቅ አባቶች እንዲሁም የተለያዩ የታሪክ ሰነዶች ያረጋግጣሉ። በዚህ መሰረት ራያ በሰሜን በኩል ከእንደርታ፣ በምስራቅ ከአፋር፣ በደቡብ ከወሎ፣ እንዲሁም በምዕራብ ከአገው ህዝቦች ጋር ይዋሰናል።

https://scontent-bom1-1.xx.fbcdn.net/v/t1.15752-9/43610567_2214645528746862_7595855469218889728_n.jpg?_nc_cat=108&oh=36f35462c14e2ab0418242328faa88fe&oe=5C47BD66 

የራያ መሬት ለእርሻ እና ለእንስሳት እርባታ ሙቹና ለም የሆነ መሬት ነው። የአየር ፀባዩም ቆላ፣ ደጋና ወይና ደጋ ተብሎ በሶስት የሚከፈል ሲሆን የተለያዩ የሰብል እና የአትክልት ምርቶችን በዋናነት ደግሞ ጤፍ፣ ማሽላ፣ ስንዴ፣ ገብስ፣ በቆሎ፣ ዓተር፣ አፕል፣ ፓፓያ፣ ዘይቱን፣ ወይን ወዘተ ይመረትበታል።
የራያ ህዝብ ከአሁን በፊት በነበሩት የማዕከላዊ መንግስታት ስርዓቶች (በዋናነት በሃፀይ ሃይለስላሴ ጊዜ) ትግራዋይ በመሆናቸው ብቻ ብዙ በደል፣ጭቆና፣ ግድያ እና አፈና ይደርስባቸው ነበር። በዚህ መሰረት ከወጀራት፣እንደርታ፣ ተምቤን፣ እንዲሁም ከሌሎች ወንድሞቻቸው ጋር በመተባበር “ቐዳማይ ወያነ” በመመስረት ራስን በራስ የማስተዳደር መብት ጥያቄ በማንሳት ከማዕከላዊ መንግስት ጋር ተዋግቷል፣ ብዙ አባቶቻችንም መስዋእት ከፍሏል።  በዚህ መሰረት የራያ ህዝብ “ከፋፍለህ እና አደህይተህ ካልሆነ በስተቀር ሊገዛ የሚችል ህዝብ አይደለም” በሚል ጨቋኝ አስተሳሰብ ግማሹ ወደ ትግራይ ግማሹ ደግሞ ወደ ወሎ ክፍለ-ሀገር በሁለት እንዲከፈል ተደርጓል።
በዚህ መሰረት የማዕከላዊ ስታትስቲካል ኤጀንሲ በ2007 እ.አ.አ ባካሄደው የህዝብና የቤት ቆጠራ መሰረት በራያ አከባቢ (ከአልውሃ ምላሽ ድረስ) ያለው ጠቅላላ የህዝብ ብዛት 836,320 ሲሆን 614,362 (73.46%)  በትግራይ ክልል ስር ሲተዳደር 221,958 (26.54%) ደግሞ በአማራ ክልል ይተዳደራል። በፆታ ደረጃ ደግሞ በግራፍ 1 ላይ  እንደሚከተለው ቀርቧል።



 ምንጭ፥ የማዕከላዊ ስታቲስቲካል ኤጀንሲ የቤቶች እና ህዝብ ቆጠራ፣ 2007 (እ.አ.አ)
 
ምንጭ፣ በትግራይ ክልል ደቡባዊ ዞን ውስጥ የሚገኙ የብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች ብዛት( ይህ ቁጥር ስሓርት ሳምረ ወረዳ እና የተወሰኑ እንደርታ ቀበሌዎች ያካትታል)።
ከላይ ያለው ግራፍ (ግራፍ 2) እንደሚያሳየው በትግራይ ክልል በኩል ካለው የራያ ጠቅላላ ህዝብ 6,369 (0.63%) አፋርኛ፣ 875 (0.1%) አገው-አውጊንኛ፣ 10,150 (1%) አገው-ክምርንኛ፣ 56,135 (5.6%) አማርኛ፣ 748(0.1%) አሪኛ፣ 612 (0.1%) ኦሮምኛ፣ 930,912 (92.5%) ትግርኛ እንዲሁም 703 (0.1%) ደግሞ የሌሎች ቋንቋ ተናጋሪዎች ይገኙበታል። በዚህ መሰረት የራያ አከባቢ የተለያዩ ብሔር ብሄረ ሰቦች እና ህዝቦች ለዘመናት በአንድነት ተከባብረውና ተፋቅረው የኖሩበት አከባቢ ሲሆን ዘጠኝ አስረኛው ህዝብ የትግርኛ ተናጋሪ ማህበረሰብ መሆኑን በግልጽ ያሳያል።
ከዚህ በተጨማሪ ከትግራይ ክልል ፋይናንስ ቢሮ የተገኘው መረጃ እንደሚያሳየው በ2011 ዓ.ም በራያ አከባቢ (ማለትም በትግራይ ክልል በኩል ያለውን) የሚኖር የህዝብ ብዛት 944,510 ሲሆን በየወረዳው እንደሚከተለው ተቀምጧል።
2. በራያ አከባቢ የሚነሱ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች
የራያ አከባቢ በትግራይ ክልል መንግስት የልማት ቀጠና (ኮሪደር) ተብሎ ከተሰየሙ አከባቢዎች አንዱ ነው። ይሁን እንጂ ከወረቀት የዘለለ በተግባር ላይ የልማት ቀጠና ሲሆን አይታይም። ስለሆነም ከዚህ በታች የተዘረዘሩትን የመልካም አስተዳደር እና የልማት ችግሮች በራያ ህዝብ በተደጋጋሚ የሚነሱና አፋጣኝ መፍትሔ የሚሹ ጉዳዮች ናቸው።
1.  የራያ ህዝብ ትናንትና ከነበሩት ጨቋኝ መንግስታት ባልተናነሰ ሁኔታ አሁንም በመሰረተ ልማት ችግሮች (በተለይ የውሃ፣ የመብራት፣ የመንገድ ወ.ዘ.ተ) እየተሰቃየ ይገኛል። ስለዚህ የመሰረተ ልማት ችግሮቹ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት ቢሰራ፣ 
2.  የራያ አከባቢ (በተለይ ቆላማው አከባቢ) በተደጋጋሚ ለድርቅ እየተጋለጠ ይገኛል። ስለሆነም ይህ ችግር ለመፍታት ይረዳ ዘንድ ብዙዎች ተስፋ የጣሉበትን የጎልጎል ራያ የልማት ፕሮጄክት በሙሉ አቅሙ በአፋጣኝ ወደ ተግባር እንዲገባ ቢደረግ፣
3.  አመራር የዕድገት የጀርባ አጥንት መሆኑን ይታወቃል። ይሁን እንጂ በራያ አከባቢ እስከአሁን ድረስ ብቁ የሆኑ መሪዎች አግኝቶ አያውቅም። በዚህ መሰረት በየደረጃው የሚቀመጡ አመራሮች የህብረተሰቡ ስነ-ልቦና፣ ባህል እና የአኗኗር ሁኔታ የሚያውቁና በህዝብ ዘንድ ተቀባይነት ያላቸው ቢሆኑ።
4.  በለስ(ቖላባሕሪ) በራያ ህዝብ ዘንድ በክረምት ጊዜ (ለ4 ወራት ያህል) ለምግብነትና ለእንስሳት መኖ ስለሚያገልግል የድሃ አባት እየተባለ ይጠራል። ከምግብ እና ከመኖ አገልግሎት በተጨማሪ መሬት በጎርፍ እና በንፋስ እንዳይሸረሸር ይከላከላል። ይሁን እንጂ በባለሙያዎችና በክልሉ መንግስት አመራሮች ቸልተኝነት እንዲጠፋ ተደርጓል።  ህዝቡ በተደጋጋሚ ቅሬታዎች ቢያቀርብም እስከ አሁን ምንም ዓይነት መፍትሔ አልተሰጠዉም። ስለሆነም የደረሰው ጉዳት በጣም ከፍተኛ በመሆኑ መልሶ የማልማት ስራ እንዲሰራበት እና ማካካሻ ሊሆኑ የሚችሉ የልማት ተቋማት ቢሰሩ።
5.  ወጣቶች የነገ ሀገር ተረካቢዎች ናቸው። የነገ መሰረቱ ደሞ ዛሬ ነው። ስለዚህ ወጣቶች ችግር አባራሪ እንጂ በችግር ተባራሪ መሆን የለባቸውም። ይሁን እንጂ የራያ ወጣቶች ከሌላው የትግራይ አከባቢ በከፋ ሁኔታ በሥራ እጦት ምክንያት ወደ ተለያዩ የአረብ ሀገራት በህገ-ወጥ መንገድ እየተጓዙ ብዙዎቹን የጅብና የዓሳ እራት እየሆኑ ነው። ስለሆነም ካለው ሽግር አንፃር ወጣቶቹ ዘለቄታዊና ቀጣይነት ባለው መልኩ ህይወታቸው የሚቀይሩበት የስራ ዕድል ቢመቻችላቸው።
6.  ከኢንቨስትመንት ጋር ተያይዞ ያለው የመሬት አሰጣጥና የካሳ ጉዳይ እንዲሁም የሊዝ ጫረታ ሁኔታ ህዝቡ ባሳተፈና በመተማመን መሆን ይገባል። ከዚህ በተጨማሪም አብዛኞቹ ኢንቨስተሮች ከገበሬው ባልተሻለ መንገድ እየሰሩ የቅሬታ ምንጭ እየሆኑ ስለሆነ መንግስት በአግባቡ የማያለሙ ባለሃብቶቸን የእርምት እርምጃ ቢወስድ።
7.  በራያ አከባቢ የሚነገረው የትግርኛ ቋንቋ በሌሎች የትግራይ አከባቢዎች ከሚነገረው አንፃር የተወሰኑ ልዩነቶች እንዳሉት ይታወቃል። ስለሆነም በልጆቹ በተወሰነ መልኩ የራሱ የሆነ ተፅዕኖ እየፈጠረባቸው ስለሆነ ትግርኛ (የራያ ዘይቤ) በሚድያ እንዲሁም በስርዓተ ትምህርት ላይ እንዲካተት ቢደረግ፣
8.  ትግርኛ ያስቸግርናል ብለው የሚናገሩ የተወሰኑ የህብረተሰብ ክፍሎች ስላሉ ይህንን ሁኔታ ተገቢው ፍተሻ ቢደረግበት።
9.  ባህል የአንድን ህብረተሰብ የማንነት መገለጫዎች መካከል አንዱ መሆኑን ይታወቃል። በዚህ መሰረት የራያ ባህል እንዲጎለብት እና የቱርስት መስህብ እንዲሆን ለማድረግ ህብረተሰቡ በማሳተፍ የራያ የባህል ማዕከል እንዲገነባ ቢያደርግ። ከዚህ በተጨማሪ የራያ አከባቢ ብዙ ባህላዊ (ለምሳሌ ቓርሻ፣ ሕቑፎይ፣ ግድል ወ.ዘ.ተ)፣ ሃይማኖታዊ (ማህበረ በኩሪ፣ ኣባ ጉባ፣ መስጊድ ወራባየ ወ.ዘ.ተ) እና የተፈጥሮ መስህቦች (ለምሳሌ ፅበት፣ ሓሸንገ፣ ሕጉምብርዳ፣ ግራኻሕሱ ወ.ዘ.ተ) ተለይተው በዞኑ ባህልና ቱሪዝም ፅህፈት ቤት ተዘጋጅተው በሚድያ በማስተላለፍ የግንዛቤ ማስጨበጫ ፕሮግራሞች እንዲዘጋጁ ቢደረግ፣

3. “የራያ የማንነት ጉዳይ”?
ቅድም ለመግለፅ እንደተሞከረው 92.5 % ያራያ ህዝብ ትግርኛ ተናጋሪ ነው። ሁኔታው እንዲህ ሁኖ ሳለ አንዳንድ የፖለቲካ ቁማርተኞች ራየታይ የማንነት ችግር አለኝ ብሎ ሳያነሳ ለራሳቸው የፖለቲካ ፍጆታ   “ራየታይ የማንነት ችግር” እንዳለው በማስመሰል የህዝቡ ሞራል በሚነካ መልኩ “ራያ አማራ ነው” “ራየ ትግራዋይ አይደለም” በማለት እርስበርሳቸው ተመራርጠው “የራያ የማንነት አስመላሽ ኮሚቴ” ብለው በመሰየም የህዝብ ጥያቄ በማስመሰል በተለያዩ የሚድያዎች አውታሮች ህዝቡን ለማወናበድ ጥረት ሲያደርጉ ይስተዋላል።
ይሁን እንጂ እኛ የራያ ተወላጆች ይህ ጥያቄ የራያ ህዝብ ጥያቄ እንዳልሆነ ስለምናውቅ፣ እንደዚህ ዓይነት ጥያቄ የሚያነሱ ሰዎች ደግሞ ልቦና ገዝተው ይመለሳሉ ብለን በማሰብ እስከአሁን ድረስ በተደራጀ መልኩ መልስ ሳንሰጥ ቆይተናል። ይሁን እንጂ “ውሸት ሲደጋገም እውነት ይመስላል” እንደሚባለው በራያ ህዝብ ስም ላይ የሚደረገውን የፖለቲካ አሻጥር እንዲቆም እና ሁሉም የኢትዮጵያ ህዝብ እንዲያውቀው በማለት እኛ (የራያ ተወላጆች) የራሳችን አቋም እንደሚከተለው እናቀርባለን። 
1.  ግለሰቦች የራሳቸው ማንነታቸው በግላቸው መወሰን ይችላሉ። ይሁን እንጂ በራያ ህዝብ ስም የሚነግዱ አንዳንድ የፖለቲካ ቁማርተኞች የግል አጀንዳቸው ይዘው የህዝብ ጥያቄ በማስመሰል ለግል ጥቅማቸው ብቻ በማሰብ የህዝብ ማንነት ወደ ገበያ በማውጣት የራሳቸው ስምና ዝና ለማሳደግ እየጣሩ ይገኛሉ። ስለሆነም “የራያ ህዝብ ማንነት ችግር” የሚባለው የተወሰኑ የግለሰቦች የማንነት ቀውስ እንጂ የህዝብ አቋም እንዳልሆነ ሊታወቅ ይገባል።
2.  “ራያ የማንነት ችግር አለበት” እንኳ ከተባለ ህገ-መንግስታዊ ስርዓቱን ተከትሎ ነበር መቅረብ የነበረበት። ይህ በእንዲህ እንዳለ ጥያቄውስ ለምን እስከ አሁን አልተነሳም ነበር? ማን ነውስ ማንሳት ያለበት? እንዴት? የሚሉትን ጥያቄዎች በአግባቡ መመለስ ያለባቸው ጉዳዮች ናቸው።  ስለሆነም የራያ ህዝብ መልካም ስሙ ለማጉደፍ የሚደረግ ዘመቻ በአፋጣኝ መቆም አለበት።
3.  ሚድያዎችም ደግሞ የግለሰብ የማንነት (Individual identity) ጥያቄ እና የህብረተሰብ የማንነት (Collective identity) ጥያቄ መለየት ያቃታቸው እስኪመስል ድረስ የአንዳንድ ግለሰቦች ሃሳብ ብቻ በመያዝ ታሪካዊውና ስነልቦናዊ ሁኔታዎች ሳያጣሩ፣ ግልፀኝነት በጎደለው አኳሃን ዘገባዎች በመስራት ህብረተሰቡ ላይ ውዥንብር በመፍጠር ለዘመናት አብሮ የኖረውን ህብረተሰብ እንዳይተማመን እና በጎርጥ እንዲተያይ ብሎም ራያ የብጥብጥ ማዕከል እንዲሆን ከሚያደርጉት አፍራሽ ድርጊቶች እንዲቆጠቡና እውነታውን ህብረተሰቡ ድረስ በመውረድ የማጣራት እውነተኛውን ዘገባ እንዲሰሩ ለማለት እንወዳለን።


No comments: