Thursday 1 November 2018

የቀለም ቅብ ስራና ኢህአዴግ

ፍስሃ መረሳ

ኢህአዴግ በፅኑ መታመሞ ከጀመረ ሰንብተዋል ፡፡ የድርጅቱ መታመም ድምር ውጤቱ እያንዳንዱ የግንባሩ አባላት ለተሰለፉለት አላማ ለማሳካት በብቃት መምራት አቅቷቸው ህዝቡ አመኔታ በማጣቱ የተነሳ አገሪቱ ወደ ቀውስ እንድትገባ አድርጓታል ፡፡ የመጨረሻ ውጤቱም እንዳየነው አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ሃይል ያልሆነ ግና በስመ ኢህአዴግ የሚነግድ ቡድን አጋጣሚውን ተጠቅሞ ስልጣኑን ተረክቦ ድርጅቱን ለማፍረስ በይፋ ሲንቀሳቀስ እንደቆየ መላው የኢትዮጵያ ህዝብ የሚያውቀው ጉዳይ ነው፡፡ እስቲ ጉዳዩ በበለጠ ለመረዳት እንዲጠቅም የተወሰኑ ጉዳዮች እንደ ማሳያ እናንሳ -
እስከኣሁን ኢህአዴግ ለማንቋሸሽና በህዝብ እንዲጠላ ከፍተኛ እንቅስቃሴ ተካሂዷል::
ኢህአዴግ እንደ ድርጅት ራሱ በፈጠረው የአመራር ጉድለት ባለፉት ጥቂት አመታት በህዝብ ቀላል የማይባል ቅሬታ እንደፈጠረ የማይካድ ሆኖ ከፈጠረው ጉድለት በላይ ግና በአገሪቱ በማንኛውም ጊዜ ያልታየና ያልተመዘገበ አለም የመሰከረለት ተጨባጭ ለውጥ እንዳመጣ ማንም የማይካደው ሃቅ ነው ፡፡ ታድያ ሃቁ ይህ መሆኑ እየታወቀ አዲሱ ስልጣን የተቆጣጠረው ሃይል ቅድሚያ ስራው በማድረግ ለምንድነው ኢህአዴግን ለማጥላላት የተነሳው የሚል በኣግባቡ መመለስ ያስፈልጋል ፡፡
ከኢህአዴግ አብራክ ወጥቻለሁ የሚል ኣዲሱ ሃይል የተሰራውን ስራ በማንቋሸሽ መልካም ስራውን በመተው በቅብብሎሽ አንዱ ኢህአዴግ በአደባባይ በተጠሩ ሰልፎችና በህዝብ ተወካዮች መድረክ ሳይቀር አሸባሪ መንግሥት እንደሆነና ለህዝቡ የረባ ስራ እንዳልሰራ እንድያውም በህዝቡ ፊት መጠየቅ እንዳለበት ያለምንም ሕፍረት በህዝብ ፊት በውጭ አገርም በውስጥም ሳይቀር ራሱ በተቆጣጠረው ሚድያ ነጋ ጠባ ያለማቋረጥ በስፋትና ባለማቋረጥ ዘምቷል ፡፡ ዘመቻው በተቀነባበረ መንገዱ ለማስፈፀም እንዲመቸው መልእክቱ በሌላ የራሱ ክልል በሚመራ የግንባሩ አባል በሆነው ድርጅት ብአዴን በሚያሳፍር መንገድ ያለፉት 27 ዓመታት የነበረው ጊዜ የጨለማና ህዝቦች በኣስከፊ ሂወት ያሳለፉት እንደነበረና አሁን ህዝቡና ራሱ አመራር በመጣው ለውጥን ነፃ እንደወጣ በተመሳሳይ መንገድ ፀረ ኢህአዴግ ዘመቻው በይፋ በከፍተኛ የድርጅቱ አመራር መልእክት እንዲተላለፍ በማድረግ ከእንግዲህ በኋላ ይህ ድርጅት መጥፋት እንዳለበት በአደባባይ ለህዝብ በግላጭ ጥሪ በማቅረብ ድርጅቱን ለማፍረስ እስከኣሁን በሙሉ ዓቅሙ በመስራት ላይ ይገኛል ፡፡ 

ሰለዚህ ይህ ሃይል ኢህአዴግ በህዝብ እንዲጠላ ከመጀመሪያው ጀምሮ ታጥቆ ሌት ተቀን የሰራ ህዝቡን ለማታለል ካልሆነ በስተቀር እንዴት ብሎ ነው አሁን ትናንት የኮነነውና እንዲጠፋለት የሚፈልገውን ድርጅት ተመልሶ ይቅርታ እንኳን ሳይጠይቅ የኔ ነው ሊል የሚችለው ? ይህ ቡድን ለይስሙላ ካልሆነ በስተቀር በፍፁም አሁን ኢህአዴግ ሊሆን እንደማይሆን ከዚህ በላይ ምን ማስረጃ ሊቀርብ ይችላል ተብሎ ይታሰባል ፡፡ ለውጡ በኢህአዴግ እንዳልመጣ በግልፅ አቋም የወሰደ አመራር አሁን ተመልሶ በፍፁም ኢህአዴግ ሊሆን አይችልምና ፡፡
የአገሪቱ ስልጣን የተቆጣጠረው ቡድን ከመነሻው ጀምሮ የተረከበው ስልጣ ኢህአዴግ እንደ ድርጅት በተሰጠው የህዝብ ሃላፊነት መሰረት ለውጡን ለማስቀጠል ብሎ የራሱን ብቁ አመራር ወደ ስልጣን እንዳመጣ በማመን ስልጣን እንደተረከበ ሳይሆን ህዝብ በተለይ ቄሮና ፋኖ ባደረጉት ከፍተኛ ትግልና በከፈሉት መስዋእትነት ስልጣን እንደያዘና ኢህአዴግ ተገዶና በህዝብ ተገፍቶ ስልጣን እንዳስረከበ እስከ ለውጡን ያመጡት ጥቂት በነሱ አጠራር ቆራጥ አመራሮች እንዳመጡት በመግለፅ በአደባባይ የነ ቲም ለማ ፎቶግራፍ በማውጣት በአንፃሩ የአብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ሃይሉ ፀረ ለውጥ የቀን ጅቦች ፀጉር ልውጥ ወዘተ እየተባለ እንዲጠፋ ብዙ ቅስቀሳና ወከባ እንደተካሄደ ይታወቃል ፡፡ ሰለዚህ ለውጡ አንዳንዴ የአንድ ግለሰብ ሌላ ጊዜ ደግሞ የተወሰኑ አመራር ያመጡት እንጂ ኢህአዴግ ለውጥ ፈላጊ ሳይሆን ኀላ ቀርና ፀረ ለውጥ ነው በማለት በግልፅ የተፈረጀ ድርጅት ታድያ አሁን ያለውን ተቃውሞ ለማርገብና አመቺ ጊዜ ለማግኘት ካልታሰበ በስተቀር በየትኛው መለኪያ ነው ይህ ሃይል ኢህአዴግ ያመጣው ለውጥ ሰለሆነ መስመሩ ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ብሎ ሊቀበል የሚችል ?
ህገመንግስታዊ ስርአቱ በግልፅ የጣሰ ሃይል የኢህአዴግ ፕሮግራም ማስቀጠል አይችልም::
ይህ ራሱን የለውጥ ሃይል ነኝ ብሎ የሚጠራ ሃይል የራሱን ፍላጎት ለሟሟላት ሲል የመጀመሪያ ስራ ያደረገው ህገመንግስታዊ ስርአቱን መጣስና እንዳይከበር ማድረግ
ነው ፡፡ ለአመታት በኢትዮጵያ ህዝቦች የተገባው ስርዓት የፖለቲካ ምህዳሩን ለማስፋት በሚል ሰበብ የዜጎች ሰላምና ድህንነት አደጋ ውስጥ በመክተት መንግሥት ባለበት አገር ያለ ጥፋታቸው በነዚህ የለውጥ ሃይል ናቸውና የፈለጉት ማድረግ ይችላሉ ተብሎው ሙሉ ፍቃድ የተሰጣቸው ፀረ ህዝብ የተደራጁ ቡድኖች በጠራራ ፀሃይ እንዲገደሉና እንዲገረፉ ህፃናትና እናቶች እንዲደፈሩ ከቤት ንብረታቸው እንዲፈናቀሉ ተደርጓል ፡፡ በስመ መደመር አንተ አልተደመርክም ስልጣን ልቀቅ እየተባለ ህገ መንግሥታዊ ስርአቱን በመጣስ ሉአላዊ ክልሎች ሳይቀሩ በፀጥታ ሃይል ቁጥጥር በማስገባት የፌዴራል ስርአቱን ለማፍረስና ፀረ ኢህአዴግ ፕሮግራም የሆነው አሃዳዊ ስርአት ለመትከል ምን ያልተሰራ ነገር አለ ? እና ኢህአዴግ ለአመታት የታገለለትና ከባድ መስዋዕትነት የከፈለለት በህዝቦች እኩልነት የተመሰረተ ፌደራላዊ ስርዓት ለማፍረስ ያለውን ሃይል ተጠቅሞ እየተረባረበ ያለው ሃይል እንዴት ብሎ ነው አሁን እወቁልኝ የኔ አሰላለፍ ከኢህአዴግ ጎን ነው ሊል የሚችለው ? ለጊዜው የፖለቲካ ትርፍ ማግኘት ካልሆነ በየአደባባዩ ህገመንግስታዊ ስርአቱ ይከበር ብሎ ለተነሳ ህዝብና ድርጅት እየኮነነ ባገኘው አጋጣሚ እያጠቃ የመጣ ሃይል በእውነቱ ለኢህአዴግ ፕሮግራም ሊታገልና መስዋዕት ሊከፍል እንደማይችል ምንም ጥርጥር የለውም፡፡
ታድያ አሁን ምን እየተባለ ነው ?
በቅርቡ የኢህአዴግ ጉባኤ ተካሂዶ አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ መስመር አሸንፎ ወጥተዋል ከዛ ውጭ አመራጭ የለም ለውጡም በኢህአዴግ የመጣ ነው ትልቅ ድል ተመዝግቧል ወዘተርፈ…..  እየተባለ ዳግም አዲስ ቅስቀሳ በመካሄድ እንዳለ ትናንት ድርጅቱን ለማጥላላት የዘመተው ሚድያው ሳይቀር ያለፈውን ስራውን ረስቶ ሰለ ድርጅቱ ከአንገት በላይ በሆነ መልኩ ከአለቆቹ የተሰጠውን ትእዛዝ ተቀብሎ በኢህአዴግ ቤት የቀለም ቅብ ስራውን ባሸበረቀ ቀለም ድርጅቱ እንዳለ ለማስመሰል ብዙ የስብከት ስራ በመስራት ላይ ይገኛል ፡፡ እዚህ ላይ ለማስመር የተፈለገው ነገር በተለይ አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ሃይሎች ኢህአዴግ ስሙ ተደጋግሞ ስለተነሳ ወይ በባነር ደምቆ ስለተፃፈ ሳይሆን በተግባር በኢትዮጵያ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዘቦች ሂወት ላይ እየመጣ ያለው ለውጥ በመምዘን ህገመንግስታዊ ስርአቱ በማክበርና የአገሪቱን ሰላምና ድህንነት በማስከበር የመጣ ተጨባጭ ለውጥ መኖሩና አለመኖሩን ከማረጋገጥ ውጪ ደመቅ ያለ ጭብጨባ ታጅቦ በአዳራሽ ተወስኗል በሚል ሁኔታውን መቀበል ራስህን በማታለል የህዝቡን ትግል ከመግደል ውጪ የሚፈይደው ነገር እንደሌለ መገንዘብ ያስፈልጋል ፡፡

No comments: