Wednesday 26 December 2018

የኢትዪ-ኤርትራ ስምምነት ‹‹የሰላም ፍላጎት›› ወይስ ‹‹የብቀላና የፖለቲካ ትርፍ ስሌት›› ?

ከ"አ/ገ"

እንደሚታወቀው ከ9 ወራት በፊት ጠ/ሚ አብይ አህመድ ወደ ስልጣን በመጡ ቅጽበት የአልጀርሱን ስምምነት ‹‹ያለ ምንም ቅደመ ሁኔታ›› ተቀብለናል በማለት ለኤርትራው መሪ ባስተላለፉት መልዕከት የተጀመረውን ሂደት እሰከ ቅርብ ግዜ ድረስ በከፊል ቅሬታና ይሆንታ ስመለከተው ቆይቼ ነበር፡፡ ሆኖም ግን ‹‹ጉድና ጅራት ከወደጭራው ነው›› እንደሚባለው የጠ/ሚ አብይን ጸረ-ተጋሩ ውቅረ ስብዕና ባረጋገጥኩኝ ግዜ በሰላም ስምምነት ሂደቱ ላይ የነበሩብኝን ቅሬታዎች በሙሉ ዘርግፌ ማቅረብ ወደድሁ፡፡ አሁን ላይ ግልጥ ሆኖ እንደሚታየኝ አብይ አህመድ የኢትዪ-ኤርትራን ስምምነት የፈለጉት ምክንያት የሁለቱ ሃገራት ህዝቦች ሰላም አሳስቧቸው እንዳልሆነ ይልቁንም ለራሳቸው የስልጣንና የፖለቲካ ትርፍ ፍጆታነት ለመጠቀም እንደነበር ፍንትው ብሎ የታየኝ ጉዳይ ሆኗል፡፡ ጠ/ሚሩ የህ.ወ.ሃ.ት ጥላቻና እና የትግራዋይ ፎቢያ በሽተኛ መሆናቸውን ካረጋገጥኩኝ በኋላ በቅንነት አልፌያቸው የነበሩ የሰላም ሂደቱ ትችቶቼን እንደሚከተለው አቀርባለው፡፡ 
የጦርነቱን መንስኤ የድንበር ግጭት አለመሆንን መጠቆም አለመቻላቸው፡፡
አስተዋይ አእምሮ ያለው ሰው ሁሉ በቀላሉ እንደሚገነዘበው ኤርትራ ኢትዪጵያን የወረረችው ባድመን ፈልጋ ሳይሆን ‹‹ጥገኛ›› የኢኮኖሚ  ‹‹ስሌቴ›› ተበጠሰብኝ በሚል የበቀል እርምጃ ለመውሰድ እንደነበር አይስተውም፡፡ ባድመ የግጭት መንስኤ እንዳልሆነች የሚከተሉትን ነጥቦች በአንክሮ በማጤን ብቻ መገንዘብ ይቻላል፡፡

a.   እ.ኢ.አ ከ 1983-90 ዓ.ም ድረስበባድመም ሆኖ በሌሎች የኢትዪ-ኤርትራ ድንበርን የተመለከተ የጎላ ችግር ሳይሰማ  ከርሞ፤ የብር ኖት ለውጥንና የኤርትራን የኢኮኖሚ ጥገኝነትን ማቋረጥ ተከትሎ የመጣ ክስተት መሆኑ፤
b.   ባድመ ያን ያህል ለግጭት የሚዳርግ የተፈጥሮ ሃብትም ሆነ ሌላ ጂኦፖለቲካዊ ፋይዳ የሌላት መሬት መሆኗ፤ በዛ ላይ የ ህ.ወ.ሃ.ት መራሹ የኢትዪጵያ መንግስት እንኳን ባድመን የምታክል ኩርማን መሬት ይቅርና መላዋን ኤርትራን ነጻ ሃገር ለማድረግ በተደረገው የትጥቅ ትግል አጋዥ ሆኖ ሲያበቃ ነጻ ሀገርነትዋ ከተረጋገጠ በኋላም እውቅና በመስጠት ከአለም ሃገሮች ሁሉ ቀዳሚ መሆኑ፡፡ ( ህ.ወ.ሃ.ት በዚህ አቋሙ ከግዛት አንድነት አቀንቃኞች ዘንድ የደረሰበትን ውግዘትና መብጠለጠል ልብ ይሏል፡፡)
c.    ኢሳያስ አፈወርቂ ‹‹ባድመ ሳይሰጠኝ ምንም አይነት ድርድር አላካሂድም!›› ብለው 18 አመት ተግትረው ቆይተው ምነው አሁን ‹‹ባድመን ውሰዱ›› ሲባሉ እምብዛም ግድ ያልሰጣቸው በርግጥም ድንበር ግጭቱ መሰረታዊ የቅራኔ መንስኤ እንዳልነበር በግልጥ አስረጂዎች ናቸው፡፡
በዚህ መሰረት አብይ አህመድ ለፖለቲካ ትርፋቸውና ለርካሽ ተወዳጅነታቸው ሲሉ ሳይጠቅሱት ያለፉት ነባራዊ ሃቅ የጦርነቱ መነሻ ድንበር አለመሆኑ ነበር፡፡ ጠ/ሚሩ እውነተኝነት ቢኖራቸው ኖሮ ቢያንስ የግጭቱ መንስኤ የእብሪተኛው የኤርትራ መንግስት ጥገኛ የኢኮኖሚ ስሌት መበጣጠስ መሆኑን የእርቅ ሂደቱን በማይጎዳ መልኩ ለዘብ ባለ የዲፕሎማሲያዊ ቋንቋ መጠቆም ነበረባቸው፡፡ ይህንን ማድረግ ያልፈለጉት የኤርትራው መሪም ሆነ ባመራር ላይ ያለው ህ.ግ.ደ.ፍ የ ህ.ወ.ሃ.ት ደመኛ ጠላት መሆኑን አበጥረው ስለሚያውቁ እርሳቸውም ( አብይ አህመድ) የነበራቸውን ‹‹ቂም›› የሚበቀሉበት ጥሩ እድል አድረገው በሚገባ ሊጠቀሙበት ስላሰቡ ነው፡፡
2.  የአልጀርሱ ስምምነት ችግር የነበረበት መሆኑን አለመጠቅሰ
የድንበር ኮሚሽኑ ውሳኔ በኢትዪጵያ መንግስት ተከራካሪ ወገኖች ንዝህላልነት ምክንያት አንድም ቀን ኤርትራን ማዕከል ባደረገ አስተዳደር ስር ተዳድራ የማታውቀውን ባድመን ለኤርትራ ሲሰጥ ስህተት መሆኑ ይታወቃል፡፡ በተጨማሪም የድንበር ኮሚሽኑ ውሳኔ የኢሮብን ህዝብ የሁለት ሃገር ሰዎች የሚያደርግ፣ አንዳንድ ቤቶችን ለሁለት የሚሰነጥቅ እና ኢትዪጵያ ያልጠየቀቻቸውን አንዳንድ የኤርትራ መንደሮች ወዲህ ማዶ ያጠቃለለ እንደነበር እየተገለጸ ይገኛል፡፡ ለዚህም ነበር የቀድሞ ጠ/ሚ መለስ ዜናዊ በነዚህ ጉዳች ላይ‹‹ የሰጥቶ መቀበል ውይይት›› ይደረግ በሚል ስልጡንና ለዘላቂ ሰላም የሚረዳ አማራጭ አቅርበው የነበረው፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ አብይ አህመድ የሰጡት ‹‹አሰብን ስንሰጥ ውይይት አላደረግንም›› የሚለው መልስ ፍጹም አላዋቂነታቸውን ወይም ለበቀል እርምጃ መቻኮላቸውን የሚያሳብቅባቸው ነበር፡፡ ሲጀምር የአሰብና የባድመ ጉዳይን የሚያመሳስለው ምንም አይነት ሁኔታ የለም፡፡ አሰብ የሄደችው ለፍትሃዊ ነጻነት ተዋግተው ድል ባደረጉ ታጋዮች ጉልበት አንጂ በውይይት አልነበረም፡፡አብይ አህመድ ‹‹ደርግን›› ወክለው እስካልተናገሩ ድረስ ደርግ አንጂ ኢ.ሃ.ዲ.ግ አሰብ አትሄድም ብሎ አንድም ሰው ወደ ጦርነት አላሰማራም፤ ይልቁንም ደግፎ ተዋጋላቸው እንጂ አልተዋጋቸውም፡፡ ስለሆነም የ ደ.ር.ግ እና የግዛት አንድነት አቀንቃኝ እንጂ ኢ.ህ.አ.ዲ.ግ አሰብን በተመለከተ ውይይት ሊያደርግ አይችልም፡፡ አብይ አህመድ ይህን ሲሉ ምን ማለታቸው እንደሆነ ግልጽ አይደለም፡፡በተጨማሪም አሰብ ኤርትራ ተብሎ የሚጠራ ግዛት አካል እንደነበረች አንጂ በተቃራኒው የሚያመላክት አንድም መረጃ አልነበረም፡፡ በተጨማሪ የአሰብ ከተማ ከኢትዪጵያ አዋሳኝ ከቶሞች ጋር የሚያስተሳስራት ምንም የ ሰጥቶ መቀበል ድርድር የሚነሳበት ምክንያት የለም፡፡ ስለዚህም ነው አብይ አህመድ የኢትየ-ኤርትራን ድንበር ጉዳይ ለእኩይ የ‹‹ብቀላ›› ፍጆታ እንጂ ለዘላቂ ሰላም አልፈልጉትም የምለው፡፡  
3.  በጦርነቱ የሃገርን ሉዓላዊነት ለማስከበር ለወደቁ ጀግኖች ክብር አለማሳየታቸው
በጣም በሚያሳፍር ሁኔታ አብይ አህመድ አስመራ ሄደው ያደረጉት ‹‹ሚሳኤል›› ሳይሆን ‹‹ ፍቅር›› ያሸንፋል አይነት የአማተር ፈላስፋ ንግግር በጦርነቱ የሃገር ሉዓላዊነትን ላለማስደፈር ውድ ህይወታቸውንና አካላቸውን መስዋዕት ያደረጉ ኢትያጵያውንን ሞራል የሚጎዳ ለርካሽ ተወዳጅነት ብቻ የተነገረ ትርጉም አልባ ዲስኩር ነበር፡፡ ከላይ ለማሳየት እንደሞከርኩት ይህ ጦርነት በኢኮኖሚ ጥገኝነት መበጠስ ዋና ምክንያትነት ግን ደግሞ በድንበር ይገባኛል ‹‹ሰበብ›› የተደረገ ዞሮ ዞሮ የሃገርን ሉዓላዊነት የደፈረን ወራሪ ለመመከት የተደረገ ፍትሃዊ ጦርነት ነበር፡፡ ለዚህ ጦርነት መላው የኢትዪጵያ ህዝቦች ከዳር እስከ ዳር ተንቀሳቅሰው ዋጋ ከፍለውበታል፡፡ በየትም ሃገር ከጦርነት በኋላ ባለ የእርቅና የሰላም ሂደት እንደሚደረገው ተገቢውን ክብር ለጦርነቱ ሰማዕታትና ለቀሩት የሰራዊት አባላት ሊገለጽላቸው ይገባ ነበር፡፡ ይህ አልተደረገም፤ ምክንያቱም የተፈለገው ርካሽ የግል ተወዳጅነትን ማትረፍ እንጂ በመርህና በቅንነት ላይ የተመሰረተ ዘላቂ ሰላምን ታሳቢ ያደረገ ስላልነበር ይመስለኛል፡፡
4.  የ ‹‹ህዝብ ለህዝብ ውይይት/ምክክር ይደረግ›› ሲባል የሰጡት የስላቅ/የሽሙጥ ምላሽ
አብይ አህመድ በአሜሪካው ጉብኝታቸው ከትግራይ ተወላጆች ለቀረበላቸው ፣፣ድንበርተኛ በሆኑ የኢትዪጵያና ኤርትራ ህዝቦች መካከል ምክክርና ውይይት ያስፈልጋል›› ለሚል አስተያት የሰጡት መልስ ይህ የ ‹‹ የፖለቲካ ነጋዴዎች›› ጥያቄ ነው የሚል ተራና  ጠብ ጫሪ መልስ ነበር፡፡ መቼም ቢሆን አንድ አይነት በሆኑ ግን ደግሞ በሁለት ሃገር በሚኖሩ ህዝቦች ዘንድ የድንበር ውዝግብ ሲኖር የህዝብ ለህዝብ ውይይት ይደረግ መባሉ ጥቅም እንጂ ጉዳት የለውም፡፡ ለ 18 አመታት የተቆየበትም ዋናው ምክንያት ይህው ተፈልጎ እንጂ ውሳኔውን ላለመቀበል እንዳልሆነ የቀድሞ ጠ/ሚ መለስ ዜናዊ በተደጋጋሚ ሲያስረዱ ነበር፡፡ አሁን ይህ ህዝቦቹንም የማስተራረቅ ስራ ይታሰብበት ብሎ መጠየቅ የፖለቲካ ነጋዴነት የሚያሰኝ ምንም ነገር የለበትም፡፡ ይልቁንም ጠ/ሚሩ ጉዳዪን በዘላቂነት ለመፍታት ሳይሆን ህ.ወ.ሃ.ትንና የትግራይን ህዝብ ለማክሰም ተቀባብሎ የጠበቃቸውን ኳስ ጠልዘው የበቀል ግብ ለማስቆጠር ብቻ ያለሙ የቂም ሰው መሆናቸውን ፍንትው አደርጎ የሚያሳይ ነው፡፡ ባካባቢው ያሉ ህዝቦች ድንበራችንን እንኳን እኛ ከብቶቻችን ሳይቀር ያውቁታል፤ ጉዳዪ እኛን በማወያየት የተሻለ እልባት  ያገኛል እያሉ ባሉበት ሆኔታ የ ጠ/ሚሩ መልስ ለጉዳዪ ባለቤት ህዝብ ያለቸውን ንቀትና ለበቀል እርምጃ የነበራቸውን መቻኮል ያጋልጣል፡፡
5.  ‹‹ያልተቀደሰው ጋብቻ››

አብይ አህመድ ከአምባገነኑ ኢሳያስ ጋር ያደረጉት የ ‹‹ፖለቲካ ግልሙትና›› አለም በታሪኳ አይታው የማታውቅ ይመስለኛል፡፡ በሁሉም መስክ እየተዳከመች ያለችውንና ህዝቦችዋም በመላው አለም እንደ አሸዋ የተበተኑባትን ሃገረ ኤርትራ የሚመሩት ኢሳያስ አፈወርቂ ስላላቸው አምባገነናዊ ባህርይ ለማስረዳት ብዙ ቃላት ማባከን አያስፈልገኝም፡፡ በየአጋረቱ የስደተኞች ማጎርያ በሰቆቃ ውስጥ ያሉትን ዜጎቻቸውንና ለ መሪያቸው ያለውን ጥላቻ ለመረዳት ብዙም አስቸጋሪ አይደለም፡፡ በአሁኑ ሰዓት አብዛኛው የኤርትራ ህዝብ አቶ ኢሳያስ እንዲወገዱለት እንጂ እንዲመሩት የሚፈልግ አይደለም፡፡ በቅርቡ የተባበሩት መንስታት የስደተኞች ኮሚሽን ባወጣው መረጃ መሰረት ድንበሩ ከተከፈተ ግዜ አንስቶ ባለፉት 6 ወራት 27000 ኤርትራውያን ወደ ትግራይ ገብተው የስደተኝነት ጥያቄ አቅርበዋል፡፡ ጦርነት፣ ረሃብ ወይም የተፈጥሮ አደጋ ሳያጋጥም ያለማቋረጥ ህዝቦችዋ ብዙም ወዳልበለጸገችው ትግራይ/ኢትዪጵያ የሚጎርፍባት ሃገር መሪ ‹‹ጥሩ መሪ ናቸው›› የሚያሰኝ አንዳች መከራከርያ ሊቀርብበት አይችልም፡፡ እንግዲህ አብይ አህመድ ይህን ሰው በቀይ ምንጣፍና በቀለበት ማጥለቅ ስነ ስርዓት እንግድነት ሲቀበሉት ‹‹ወያኔን›› የሚጠላ ሁሉ ሰይጣንም ቢሆንም ወዳጄ ነው እያሉን እንጂ ሌላ ምንም ሊሆን አይችልም፡፡ በተመሳሳይ መልክ የኤርትራን መሪዎች የጦርነቱ ዋና ጠበኞቹ ከሆኑት የህ.ወ.ሃ.ትና የትግራይ ክልል አመራሮች ጋር ለማቀራረብና ይቅር ለማባባል ከመሞከር ይልቅ ምንም ቅራኔ ካልነበረባቸው የአማራ ክልል መሪዎች ጋር መሞዳሞዳቸው ጠ.ሚው ይህን የኢትዪ-ኤርትረ ጉዳይ ለእውነተኛና ዘላቂ ለሆነ የሁለቱ አገሮች ሰላም ሳይሆን ለብቀላ እርምጃ፤ ‹‹ጠላቴ›› ነው ያሉትን ህ.ወ.ሃ.ትንና ህዝባዊ መሰረቱን ትግራይን ለማዳከም ያደረጉት ነው የምልበትን አመክንዪ ያጸናልኛል፡፡በጣም አሳፋሪው ግን ‹‹ወያኔ›› የሰራቸውን ግድቦችና የኢንዱስትሪ ፓርኮች ከ‹‹ወያኔ›› ጠላትና ቂመኛው አቶ ኢሳያስ ጋር ሆነው መመረቃቸው ነው፡፡ አንድ ቀን ለዚህ አሳፋሪ ውርደተ ስብዕና  በቴሌቭዥ ን የተሰራ ዶክመንተሪ እንደምናይ ተስፋ አደርጋለው፡፡

6.  የባድመ ሰላም ለ ‹‹ሳውዲና ለዱባይ›› ምናቸው ነው?

የኢትዪ-ኤርትራ ሰላም እምብዛም ከማይመለከታቸው የሳውዲና የአረብ ሃገራት ጋር የሚደረገው ምንነቱ የማይታወቅ ስምምነትና ‹‹ሽር ጉድ›› በርግጥ ለኢትዪጵያና ኤርትራ የድንበር ውዝግብ እልባት የመስጠት ፍላጎት ብቻ እንዳልሆነ ግልጽ ነው፡፡ ሳውዲ በ ኢትዪ-ኤርትራ ሰላም ምንም አይነት ቀጥተኛ ሃገራዊ ጥቅም የላትም፡፡ ይልቁንም ከሰላም ስምምነቱ በስተጀርባ ያለን ሌላ የፖለቲካ ትርፍ ስሌት እንዳለት ያመላክታል፡፡ ኢሳያስና አብይ ሳውዲ ድረስ አስጠርቶ ወርቅ ባንገታቸው የሚያስጠልቅ እርምጃ ከሰላም ስምምነቱ ጥድፊያ ጀርባ እየታቀደ ያለን ሌላ ከባድመ ውጪ ያለን ጂኦፖለቲካዊ ጥቅም ያመላክታል እንጂ ሳውዲ በኢትዪ-ኤርትራ ሰላም ‹‹ጮቤ ረገጠች›› የሚያሰኝ አንዳች አሳማኝ አመክንዪ የለም፡፡ ከወራት በፊት በጠላትነት ተፋጥው የነበሩ ወታደሮችን በማጣመር የጋራ ህብረትና የ ባህር ሃይል በቀይ ባህር ላይ የመዘርጋት ምክረ ሃሳብ በየመን ለሚካሄደው የ ቅጥር ጦርነት ለማዘጋጀት የሚደረግ መቻኮል እንጂ ወዲህ ማዶ ላለው የጉዳዪ ባለቤት የኢትዪ-ኤርትራ ድነበርተኛ ህዝብ ሊሆን ፈጽሞ አይችልም፡፡
7.  የ ህ.ወ.ሃ.ት ስህተት
በኔ እምነት የኢትዪ-ኤርትራ ጦርነት መካሄድ ያልነበረበት ‹‹ፕሪቨንተብል›› ነበር፡፡ በወቅቱ እጅግ አርቆ አስተዋይ መሪያችን መለስ ዜናዊ ጦርነቱ መካሄድ የለበትም የሚል አቋም እንደነራቸው ይታወቃል፤ ሆኖም ግን በግዜው በነበረው የቡድን አመራር ‹‹ኮሌክቲቭ ሊደርሽፕ›› መርህ መሰረት ባንላጫ ድምጽ ተወስኖ ወደ ጦርነት እንደተገባ ይታወቃል፡፡ ይህው ጦርነት ባመጣው ጦስ የህ.ወ.ሃ.ት/ኢ.ህ.አ.ዲ.ግ  ‹‹ኮሌክቲቭ ሊደርሽፕ›› መርህ ወደ አቶ መለስ ብቸኛና ጠቅላይ መሪነት መለወጡም ይታወሳል፡፡ ይህ መሆኖ ላልቀረ በወቅቱ አቶ መለስ የጠ/ሚ ስልጣናቸውን ተጠቅመው ሃገራችን ወደ ጦርነት እንዳትገባ ቢያደርጉ ኖሮ በተሻለ ነበር፡፡ የኢትዪ- ኤርትራ ጦርነት በሃገራችን ልማትና ፖለቲካዊ አስተዳደር ውስጥ አፍራሽ ተጽዕኖ ያሳረፈ፤ ኤርትራንና ኤርትራውያንንም በባሰ መልኩ የጎዳ የክፍለ ዘመናችን አሳዛኝ ታሪካዊ ክስተት ሆኖ ይዘከራል፡፡
ማጠቃለያ
‹‹የፈሰሰ ውሃ አይታፈስም›› አንዲሉ ጦርነቱ ያደረሰውን ጉዳት ሁሉ አድረሶ አልፎኣል፡፡ ወደ ኋላ ተመልሰን ማድረግ የምንችለው ምንም ነገር ባይኖርም ቀጣይ ጉዳቶችን ለማስቀረት ግን በቅንነት መስራት ያስፈልጋል፡፡ እንዳለመታደል ሆኖ ግን አሁንም የጦርነቱ ዋነኛ መንስኤና ተንኳሽ አቶ ኢሳያስ እና በ ህ.ወ.ሃ.ት/ ትግራይ ጥላቻ የተሞሉት አብይ አህመድ ጉዳዪን እንደገና ችግሮችን በሚፈታ ሳይሆን በሚያባብስና በሚያወሳሰብ ግላዊና ፖለቲካዊ የትርፍ ስሌት ስር የወደቀ ግዳይ አድርገውታል፡፡ እንግዲህ ባንድ ወቅት ብዙም ሳንመርምር በቅንነት የተቀበልነው የኢትዪ-ኤርትራ የጥድፊያ የሰላም ስምምነት የትግበራ ሩጫ አሁን ላይ የአብይ ‹‹ፈሪሃ›› ህ.ወ.ሃ.ት እና ‹‹ትግራይ ፎቢክ›› ተክለ ስብዕና ፍንትው ብሎ ሲታየን እርምጃውን በሰላ ግምገማ ስንመለከት የሚከሰትልን እውነታ ከላይ የተተነተነውን ይመስላል፡፡ ኢሳያስ ለባድመ ሲሉ አልተዋጉም ይልቁንም እንዲቋቋም የረዳሁት ‹‹ወያኔ›› እንደ ‹‹ጭሎ›› ‹‹ያልኩትን አልሰማኝም›› በሚል ‹‹የተንቄያለው አሳያለው›› ብሽቀት የከፈቱት የ‹‹ሰበብ›› ውጊያ እንደነበር፤ አብይ አህመድም ‹‹ወያኔ››ን የሚያዳክምልኝ ማንኛውም የተቀባበለ ኳስ ሁሉ እየጠልዝኩ የብቀላ ጎል ማስቆጠሬን እቀጥላለው በማለት የሄዱበት መንገድ መሆኑን በተሻለ ግልፅነጽ ለመረዳት ይቻላል፡፡ ይህን ሁሉ ክፉ ልብ የተመለከተ ‹‹ቅን ፈራጅ አምላክ›› የሁለቱን መሪዎች እኩይ ‹‹ሞቲቭ›› ከግቡ እንዳይደርስ አድርጎ መካሄድ ባልነበረበት ጦርነት ምክንያት የተፈጠረውን መቃቃር ያሽርልን ዘንድ ምኞትና ጸሎቴ ነው፡፡

____________________________

አ ፖ (AP) ተጨማሪ :
የ ኤርትራና የኢትዮጵያ ጦርነት አንድንጻ በማድረግ ተጠያቂው  ኢሳያስ አፈወርቂና ሻዕብያ ናቸው ::  መልለ ዜናዊ ጦርነቱ አንዲ ጀመር የድርሻዉን አድርጎአል :: መለስ ዜናዊ ኤርትራ ለጦርነት እየተዘጋጀች መሆኖአን አያወቀ የኢትዮጵያ ሰራዊት አንዲ ዘጋጅ አላደርገም:: አንዲያዉም የወያኔ ሰራዊት በየምክንያቱ  አንዲበተን ነው የተደረገው :: ህወሓት የኢትዮጵያን ላእላዉነት  ተከለካለች  እንጂ ጦርነቱ አንድጀመር አትፈልግም ነበር :;"ኤርትራ" ጦርነቱ እንዲነሳና  በአስከፊ   ሁኔታ እንዲ ጨረስ  አድርጋለች :; 

No comments: